በማዕከላዊ እስር ቤት የህወሃት መርማሪዎች ከፍተኛ ሰቆቃ እንደሚፈጽሙ ተገለጸ

ኢሳት (መጋቢት 14 ፥ 2008)

በማዕከላዊ እስር ቤት የህወሃት መርማሪዎች ከፍተኛ አካላዊና ሞራላዊ ሰቆቃ በታሳሪዎች ላይ እንደሚፈፅሙ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ምክትል ፕሬዚደንት የነበሩት አቶ ዘመነ ምህረቱ ገለጹ።

ከአስራ አራት ወራት እስር በኋላ ባለፈው መጋቢት 8, 2008 በዋስ የተለቀቁት አቶ ዘመነ ምህረት፣ በወህኒ ቤቶች ውስጥ ለምርመራ የተሰማሩት የህወሃት ገራፊዎች ለመናገር የሚከብድ ሰቆቃ በእርሳቸው ላይ እንደፈጸሙባቸው ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ገልጸዋል።

ምንም ወንጀል ባልፈፀሙበት ሁኔታ ከጎንደር ተይዘው አዲስ አበባ እስኪደርሱ ድረስ አይናቸው ተሸፍኖ፣ እግራቸውና እጃቸው ተጠፍሮ እንደተሰቃዩ አቶ ዘመነ በምሬት ተናግረዋል። ወህኒ ቤት እያሉም የህወሃት ገራፊዎች ሱሪያቸውን አስልወልቀው እንደሰደቧቸውና ከፍተኛ ድብደባ እንደፈጸሙባቸው አቶ ዘመነ ምህረቱ ገልጸዋል።

“ምኞትህ አማራውን ወደስልጣን ለማምጣት ነው፣ የሚኒሊክ ዘር ድጋሚ ስልጣን ላይ አይወጣም” እየተባሉ እንደተገረፉና፣ የህወሃት መርማሪዎች ሱሪያቸውን አስወልቀው ሽንት እንደሸኑባቸው ይህም አስጸያፊ ድርጊት ሞራላቸውን እንደጎዳቸው አቶ ዘመነ ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ተናግረዋል።

በማዕከላዊ ምርመራ ያሉ ሁሉም ገራፊዎች ትግረኛ ተናጋሪዎች እንደሆኑ የገለጹት አቶ ዘመነ፣ ሱሪ ካስወለቁ በኋላ ለምን እንደሚደበድቡኝ ስጠይቅ የአማራን ሞራል ለመስበር የምንጠቀምበት ዘዴ ነው በለው እንደነገሯቸው አቶ ዘመነ በስልክ ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ተናግረዋል። አማራ የተባለውን ሁሉ ሱሪ እያስወለቁ እንደሚገርፉና ዘርን የሚያንቋሽሽ ስድብ እንደሚሳደቡም ጨምረው ገልጸዋል።

“አሁን የተረዳሁት ከአማራ ብሄረሰብ መወለድ ወንጀል መሆኑን ነው” ያሉት አቶ ዘመነ፣ በማዕከላዊ እያሉ ብዙ ነገር እንደተማሩና ሰዎች በሰሩት ወንጀል ሳይሆን በአማራነታቸው ብቻ ምርመራ እንደሚደረግባቸው ለኢሳት ገልጸዋል። ስለህወሃት ሰዎች የተሳሳተ ግንዛቤ እንደነበራቸውም ያልሸሸጉት አቶ ዘመነ፣ “ የህወሃት ሰዎች እንዲህ የሚያደርጋቸው የስልጣን ፍላጎት ይመስለኝ ነበር፣ አሁን እንደተረዳሁት ግን የዘር ጥላቻ ነው” ብለዋል።

ህይወታቸው አደጋ ላይ ያሉ ሰዎች አማራ በመሆናቸው ብቻ ህክምና እንደማያገኙና እሳቸው የሚያቁት አንድ ሰው በ4 ጥይት ሆዱ ላይ ተመትቶ ጥይቶቹን ከሆድ ውስጥ ለማውጣት ቢጠይቅም የወህኒ ቤቱ አስተዳደር አሸባሪ በመሆኑ አይታከምም ብለው እንደከለከሉም አቶ ዘመነ ምህረቱ በምሬት ገልጸዋል።

የማዕከላዊ ገራፊዎች “ታማኝ ተቃዋሚ ሆነህ ከሰራህ ድጋፍ እናደርግልሃለን፣ አይሆንም ካልክ ፕሮፌሰር አስራትንና አንዷለም አራጌን እንዳሰርነው አንተም ወህኔ ቤት ትበሰብሳለህ” እንዳሉት አቶ ዘመነ ተናግረዋል።