በኦሮሚያ ክልል የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ለሶስተኛ ቀን ቀጥሎ መዋሉ ተሰማ

(ኢሳት ዜና–ጥቅምት 3/2010) በኦሮሚያ ክልል የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ለሶስተኛ ቀን ቀጥሎ መዋሉ ተሰማ።

በተለይም በምዕራብና ምስራቅ ወለጋ ህዝባዊ ተቃውሞ በበርካታ ከተሞች የተካሄደ ሲሆን በቡሌ ሆራ ዩኒቨርስቲ ተቃውሞው ጠንካራ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል።

በወለጋ ጊምቢ የተካሄደው ተቃውሞ በብዙ ሺህ የሚቆጠር የከተማዋ ነዋሪ የታደመበት ሲሆን የህወሀት መንግስት ከስልጣን እንዲወርድም ተጠይቋል።

ሆለታ፣ በሀረርጌ ኮምቦልቻ ተቃውሞ ከተካሄደባቸው አካባቢዎች የሚጠቀሱ ሲሆን ባለፈው ረቡዕ ዘጠኝ ሰዎች ወደ ተገደሉባት ሻሸመኔ ተጨማሪ የፌደራል ሃይል እንዲገባ መደረጉ ታውቋል።

ሶስተኛ ቀኑን የያዘው የኦሮሚያ ክልል ተቃውሞ አድማሱን እያሰፋ ሌሎች ከተሞችንና መንደሮችን እየጨመረ ቀጥሏል።

በምዕራብና ምስራቅ ወለጋ በዛሬው ተቃውሞ በርካታ ከተሞች ተሳታፊ ሆነዋል።

ትላንት በነቀምት የተጀመረው ተቃውሞ ዛሬም ቀጥሎ በስልጣን ላይ ላለው የህወሀት መንግስት ግልጽ መልዕክት የተላለፈበት ሆኖ ተጠናቋል።

የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ የውጭ ድጋፍ ሰብሳቢ አቶ ነጌሶ ኦዳ ለኢሳት እንደገለጹት ከረቡ ጀምሮ እየተካሄደ ያለው ተቃውሞ በዋናነት ሁለት መልዕክቶችን የማስተላለፍ አላማ አንግቧል።

በዛሬው ተቃውሞ ከተሳተፉት አካባቢዎች የቡሌ ሆራ (ሀገረማርያም) ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ያደረጉት ከስርዓቱ ታጣቂዎች ጋር ግጭትን የፈጠረ ነበር።

ተማሪዎች በአመጽ የዩኒቨርሲቲውን ቅጥር ግቢ በማጥለቅለቅ ተቃውሞ ሲያሰሙ የስርዓቱ ታጣቂዎች የሃይል እርምጃ መውሰዳቸውንና በርካታ ተማሪዎች መጎዳታቸውን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

ትላንት በቦረና ዲሬ ወረዳ ስድስት ሰዎች በህወሀት ሰራዊት መገደላቸውን ተከትሎ እስከሞያሌ ያለው መንገድን ጨምሮ በዱብሉቅ፣ ያቤሎና ወደ ሌሎች ዋና ዋና ከተሞች የሚወስዱ መንገዶችም መዘጋታቸው የተገለጸ ሲሆን በቡሌ ሆራ የተፈጠረው ግጭትም በአካባቢው የሚገኙ መንገዶችን እንዲዘጉ ማድረጉን መረጃዎች ያመለክታሉ።

በወለጋ ጊምቢ የተካሄደው በከተማዋ ታሪክ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህዝብ የተሳተፈበት ሲሆን የተቃውሞው ማሳረጊያ መልዕክትም የህወሀት መንግስት በአስቸኳይ ከስልጣን እንዲወርድ የሚጠይቅ እንደነበረ ለማወቅ ተችሏል።

በሆለታ በተካሄደው ተቃውሞ ህዝቡ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ድረስ በመሄድ የህወሀት መንግስት በአስቸኳይ ከስልጣን እንዲወርድ በመጠየቅ ድምጻቸውን አሰምተዋል።