13 የሃይማኖት አባቶችና ካህናት በረሃ ወርደው አርበኞች ግንቦት 7ትን ተቀላቅለው ህዝብን በማስተባባር ላይ መሆናቸውን ገለጹ ።

ኅዳር ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻ / ኢሳት ዜና :- በዋልድባ ገዳም እና በተለያዩ ቤተክርስቲያኖች ሲያገለግሉ የነበሩ 13ቱ አባቶች ወደ በረሃ ለመውረድ የወሰኑት አገዛዙ በህዝብ ላይ የሚያደርሰውን ግፍ እያዩ ዝም ለማለት ህሊናቸውና ሃይማኖታቸው ስላልፈቀደ መሆኑን ተናግረዋል።

ጠመንጃ ይዘን ባንዋጋም ፣ በረሃ ወርደን ህዝቡ ለነጻነቱ እንዲነሳ እየቀሰቀስነው ነው ያሉት አባቶች፣ በረሃ ውስጥ ከአርበኞች ግንቦት7 አደራጆች ጋር ከተገናኙ በሁዋላ የኢትዮጵያ ወጣት ትግሉን እንዲቀላቀል ትምህርት በመስጠት ላይ መሆናቸውንም ገልጸዋል።

ከአርበኞች ግንቦት7 መሪ ከፕ/ር ብርሃኑ ነጋ እና ከሌሎችም የድርጅቱ መሪዎች ጋር በቅርበት በመነጋገር በአካባቢው የተጀመረው ትግል ዳር እንዲደርስ የበኩላቸውን እየተወጡ መሆኑንም አባቶቹ ተናግረዋል። የአርማጭሆና የአካባቢው ህዝብ ከጎናችን ተሰልፎ ድጋፉን እየሰጠን ነው የሚሉት ሌላ አባት፣ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ እየተቀጣጠለ የመጣውን ትግል ተቀላቅሎ የአገዛዙን እድሜ እንዲያሳጥር መልዕክት አስተላልፈዋል።

እኝህ አባት ጳጳሳትና መነኮሳት ሌላውም እንደየስጦታው ተነስቶ ይህን አሸባሪ አገዛዝ ሊያስወግደው ይገባል ብለዋል።

አባቶቹ ቀደም ብለው በሰሜን ጎንደር ሲካሄድ የነበረውን ህዝባዊ ተቃውሞ ሲያስተባባሩ  እንደነበር ይታወቃል።