ግብጽ የህዳሴው ግድብ በውሃ መሞላት አልተጀመረም አለች

(ኢሳት ዜና–ሐምሌ 7/2009)በኢትዮጵያ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ እየተባለ የሚጠራው የኣባይ ግድብ መጋቢት 24/2003 ላይ የመሰረት ድንጋዩ ሲጣል 6 ሺ ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሃይልን ማመንጨት አላማው አድርጎ ነው።

ከግድቡ ግንባታ መጀመር ጋር ተያይዞ ፍትሃዊ የሆነ የውሃ ክፍፍል ላይኖር ይችላል የሚለው ጥያቄ ደግሞ ከጎረቤት ሀገራት በተደጋጋሚ ይነሳ የነበረ ቅሬታ ነው።

የኢትዮጵያ መንግስትም የግድቡ ግንባታ ማንንም የማይጎዳና ጎረቤት ሀገራትን  ተጠቃሚ የሚያደርግበት ሁኔታ መኖሩን በጥናት ለማሳየት ሞክሯል።

ግድቡን በውሃ የመሙላቱ ስራም ጎን ለጎን የሚካሄድ ሌላኛው ተግባር እንደሚሆንም የኢትዮጵያ መንግስት ማሳወቁ ይታወሳል።

ሀገራቱ በጉዳዩ ዙሪያ ከስምምነት ላይ ይድረሱ እንጂ ከግብጽ መንግስት በየጊዜው የሚነሳው ቅሬታ ያበቃ አይመስልም።

እንደሀገሪቱ የውሃ ሃብትና የመስኖ ሚኒስቴር ገለጻ ከሆነ ኢትዮጵያ ግድቡን በውሃ የመሙላቱን ስራ እንደምትጀምር ብታሳውቅም እስካሁን ግን ተግባራዊ ማድረግ አልቻለችም። — ይህንን ደግሞ በሳተላይት መረጃዎቼ ማረጋግጥ ችያልሁ ብሏል።

እንዲያውም የሳተላይት መረጃዎቼ በወቅቱ እየጣለ ካለው ዝናብ ጋር በተያያዘ የሚፈጠረው ጎርፍ ወደ ግድቡ እንዲገባ የሚያስችል የጎርፍ ማስገቢያ መስመር በግድቡ በአንደኛው ጎን መዘጋጅቱን እንዳርጋግጥ አድርገውኛል ብሏል ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ።

ሰኔ መጨረሻ ላይ መጣል ከጀመረው ዝናብ ጋር ተያይዞ የሚፈጠረው ጎርፍ የሚቀጥለው እስከ መስከረም መጨረሻ ነው። ያ ደግሞ በአመቱ በግድቡ ሊኖር የሚገባውን የውሃ መጠን ማሟላት አይችልም ሲል አክሏል ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ።

የግድቡ ውሀ የሚሞላ ከሆነ የግብጽ መንግስት በአመቱ ለፍጆታ አውለዋለሁ የሚለውን 55 ነጥብ 5 ቢሊየን ኪዩቢክ ውሃ አደጋ ውስጥ ሊከተው ይችላል ።

የኢትዮጵያ መንግስትም የግድቡ ግንባታ በተፋሰሱ ሀገራት ላይ ምንም አይነት ጉዳት እንደሌለው አሁንም ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ሲል ምላሹን ሰቷል።

በአሁኑ ሰአት በግድቡ ውስጥ ያለው የውሃ መጠንም ቢሆን ግብጽ በአመቱ ለታገኝ የሚገባትን የውሃ ኮታ የሚጎዳ አይደልም ብሏል።

በግድቡ ያለው የሃይቅ መጠን ካለፈው አመት እየጨመረ መምጣቱ ደግሞ ምንም አይነት ስጋት እንደማይኖር ማሳያ ነው ብሏል የኢትዮጵያ መንግስት።ዘገባው የሚድል ኢስት ሞኒተር ነው።