ዶ/ር መረራ ጉዲና የቀረበባቸውን ክስ በመቃወም ለፍርድ ቤት መቃወሚያ አቀረቡ

ኢሳት (ሚያዚያ 16 ፥ 2009)

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተላልፈዋል ተብለው የታሰሩትና ህገ-መንስታዊውን ስርዓት በሃይል ለመናድ በሚል በእስር የሚገኙት ዶ/ር መረራ ጉዲና የቀረበባቸውን ክስ በመቃወም ሰኞ ለፍርድ ቤት መቃወሚያን አቀረቡ።

ዶ/ር መረራ ጉዲና በከሳሽ አቃቤ ህግ የተመሰረተባቸውን ክስ ለመቃወም ባለ 11 ገፅ የክስ መቃወሚያን ያቀረቡ ሲሆን፣ ቤልጂየም ለህዝባዊ ስራ በሄድኩበት ጊዜ የአስቸኳይ ጊዜ ዋጁን ተላልፏል ተብሎ የቀረበውን ክስ ተዋውመዋል። ከሳሽ አቃቤ ህግ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተላልፈዋል ካለው ክስ በተጨማሪ ህገመንስቱን በሃይል ለመናድ በመሞከር የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ እንዲባባስ አድርገዋል ሲል በክሱ አመልክቶ እንደነበር ይታወሳል።

የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ (ኦፌኮ) አመራሩ የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትዎርክ ተብሎ በሚጠራው ሚዲያ ላይ ስለእሬቻም ሆነ የሁከት ጥሪ በሚመለከት ቃለምልልስ አላደረኩም ሲሉ የቀረበባቸውን ክስ እንደተቃወሙ በሃገር ውስጥ ያሉ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።

የፌዴራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ ዶ/ር መረራ ህዝባዊ ተቃውሞ እንዲባባስ በማድረግ ህገመንግስቱ በሃይል ለመናድ ተንቀሳቅሰዋል ሲል በክሱ አመልክቷል።

አቃቤ ህግ ከህዝባዊ ተቃውሞ ጋር በተገናኘ ለጠፋው የሰው ህይወትና ንብረት ተከሳሹ ተጠያቂ መሆን ይገባቸዋል ሲሉ ባቀረበባቸው ሶስት የተለያዩ ክሶች አቅርቧል።

ከሳሽ አቃቤ ህግ ዶ/ር መረራ ጉዲናን እንዲሁም በሌሉበት ክስ የተመሰረተባቸውን ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋን እንዲሁም የኦሮሞ ሚዲያ ኔትዎርክ ሃላፊ አቶ ጃዋር መሐመድን በአንድ የክስ መዘገብ ክሱን ባለፈው ወር ማቅረቡ ይታወሳል።

ይሁንና የኦፌኮ አመራሩ ክሳቸው በተናጠል እንዲታይላቸው ለፍርድ ቤት ጥያቄን ያቀረቡ ሲሆን፣ በአጠቃላይ የቀረበባቸው ክስ ዝርዝር ነገሮች ይቀሩታል ሲሉ ተቃውሞን እንዳቀረቡ ለመረዳት ተችሏል።

መቃወሚያውን የሰማው ፍርድ ቤቱም መቃወሚያ ላይ የአቃቤ ህግ አስተያየትን ለመስማት ለሚያዚያ 26 ቀን 2009 አም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

ሂማን ራይትስ ዎች ዶ/ር መረራ የቀረበባቸው ክስ ፖለቲካዊ ተልዕኮ ያለው ነው በማለት መንግስት ክሱን ውድቅ እንዲያደርግ መጠየቁ ይታወሳል።

ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ጋር በተገናኘ የኦፌኮ አመራር የሆኑት አቶ በቀለ ገርባ በተመሳሳይ ድርጊት ለእስር መዳረጋቸውም አይዘነጋም።