ዶ/ር መረራ ከእስር እንዲፈቱ የሚያስተባብር አለም ቀፍ ግብረ ሃይል ተቋቋመ

ኢሳት (ታህሳስ 21 ፥ 2009)

ነዋሪነታቸው በተለያዩ የአለማችን ሃገራት የሆነ ኢትዮጵያውያን ዶ/ር መረራ ጉዲና ከእስር እንዲፈቱ የሚያስተባብር አለም ቀፍ ግብረ ሃይል አቋቋሙ።

ግብረ ሃይሉ እያካሄደ ያለው ይኸው አለም አቀፍ ዘመቻ አሜሪካንን ጨምሮ የአውሮፓ ህብረትና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ኢትዮጵያ ለእስር የዳረገቻቸው የፖለቲካ እስረኞችና ጋዜጠኞችን እንዲሁም ሌሎች አካላትን እንድትለቅ ግፊት እንደሚያደርጉ የሚጠይቅ መሆኑ ታውቋል።

የዘመቻው መጀመር አስመልክቶ መግለጫን ያወጣው ግብረ ሃይሉ በቅርቡ ተግባራዊ ተድርጎ የሚገኘውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተላልፈዋል ተብለው ለእስር የተዳረጉት ዶ/ር መረራ ጉዲና ተይዘው ያሉበት ሁኔታ አሳሳቢ መሆኑን አስታውቀዋል።

የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ አመራሩ እጃቸው በሰንሰለት ታስሮ በጨለማ ክፍል በማዕከላዊ የምርመራ ዕስር ቤት እንግልት እየደረሰባቸው እንደሚገኝ ግብረ ሃይሉ ይገልጻል።

ትላንት ሃሙስ ለሁለተኛ ጊዜ ፍርድ ቤት ቀርበው የነበሩት ዶ/ር መረራ በሽብርተኛ ወንጀል ክስ ለመከሰስ ያበቃቸዋል የተባለ ምርመራ እየተካሄደባቸው መሆኑን ፖሊስ ለችሎት ማሳወቁን መዘገባችን ይታወሳል።

ይሁንና የኦፌኮ አመራሩ በህይወት ዘመናቸው ጸረ ሁከትና ሽብርን በማውገዝ በመምህርነት ሙያቸው ሲያገለግሉ መቆየታቸውን ለችሎቱ በማስረዳት ፖሊስ እያካሄድኩ ነው ያለውን ምርመራ አስተባብለዋል።

ዶ/ር መረራ ጉዲናን ጨምሮ በእስር የሚገኙ በሺዎች የሚቆጠሩ ታሳሪዎች እንግልትና ስቃይ እንደደረሰባቸው መሆኑን በተለያዩ መንገዶች ዝመቻውን እያካሄደ ያለው ግብረ ሃይል አክሎ ገልጿል።