ያለህዝብ ፍቃድ በፖለቲካ ውሳኔ በተከለሉት 42 ቀበሌዎች ህዝበ ውሳኔ እንዲደረግ ተጠየቀ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 8/2010) ያለህዝብ ፍቃድ በፖለቲካ ውሳኔ በተከለሉት 42 ቀበሌዎች ህዝበ ውሳኔ እንዲደረግ ተጠየቀ።

ትላንት በ8 ቀበሌዎች በተካሄደው ሕዝበ ውሳኔ 7ቱ ቀበሌዎች በነባሩ የሰሜን ጎንደር አስተዳደር ስር መቆየትን መምረጣቸው ተገልጿል።

ይህን ተከትሎም ቀደም ሲል በህወሃት መንግስት በተከለሉት 42 ቀበሌዎች ላይ ሕዝበ ውሳኔ እንዲደረግ በመጠየቅ ላይ መሆኑን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
ምርጫ ቦርድ የትላንቱን ህዝበ ውሳኔ ውጤት በፌደሬሽን ምክርቤት በኩል እንደሚገለጽ አስታውቋል።

የጎንደር ህዝብ አንድነቱን ዳግም ባስመሰከረበት የትላንቱ ህዝበ ውሳኔ ሳይዘናጋ በህወሀት መንግስት የተወሰዱትን ሌሎች አካባቢዎችንም እንዲጠይቅ ጥሪ እየተደረገ ነው።
የቅማንትን ልዩ አስተዳደር ለመትከል በሚል የተዘጋጀውና በ8ቀበሌዎች ትላንት የተደረገው ህዝበ ውሳኔ ውጤት በምርጫ ጣቢያዎች ዛሬ መለጠፋቸው ታውቋል።

በውጤቱም መሰረት ሰባቱ ቀበሌዎች በቀደመው አስተዳደር ስር መቀጠልን የመረጡ ሲሆን ኳቤር፣ ሎምየ የተባለው በጭልጋ ወረዳ የሚገኝ ቀበሌ ብቻ ቅማንት ተብሎ ሊተከል ወደታቀደው አስተዳደር ለመሆን ድምጽ መስጠቱ ነው የተገለጸው።

በአጠቃላይ የትላንቱ ህዝበ ውሳኔ የህዝብ አንድነት የታየበት፣ ሁለቱን ማህበርሰቦች ለመነጣጠል ለፈለጉ ሃይሎች ኪሳራ ሆኖ የተመዘገበበት መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ።

በስልጣን ላይ ያለው ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ የሚመራው መንግስት ቅማንትን ከአማራው ነጥሎ አስተዳደር ለመትከል ያቀደበት ምክንያት በብዙዎች ዘንድ ከታላቋ ትግራይ መስፋፋት ጋር የሚያያዙት ሲሆን የትላንቱ ህዝብ ውሳኔ ይህን ያከሸፈ እንደሆነ ይነገራል።

የአካባቢው ተወላጅ የሆኑት አቶ አበበ ንጋቱ እንደሚገልጹት የትላንቱ የህዝብ ውሳኔ ህዝብን በዘር መለያየት የትም እንደማያደርስ የተመሰከረበት፣ የገዢው ስርዓት የከፋፋይነት መስመሩ መቃብር የወረደበት መሆኑን ያሳየ ነው።

በህወሀት መንግስት በኩል የህዝበ ውሳኔው ሊገለበጥ ከቻለ ህዝብ ነቅቶ እንዲጠብቅ ጥሪ እየተደረገ ነው።
በምርጫ ቦርድ በኩል እንደተገለጸው ትላንት የተደረገው ህዝበ ውሳኔ የፊታችን መስከረም 15 ለፌደሬሽን ምክር ቤት ይቀርባል።

ውጤቱም በይፋ የሚገለጸው በፌደሬሽን ምክር ቤት አማካኝነት እንደሆነ ተገልጿል።

ከ10ዓመት በፊት በግጨው አካባቢ የተደረገውንና ከ90በመቶ በላይ የሚሆነው ህዝብ በአማራ አስተዳደር ስር መቆየትን የመረጠበት ህዝበ ውሳኔ ውጤቱ ሳይገለጽ በፌዴሬሽን ምክር ቤት ተቆልፎበት እንደሚገኝ የሚጠቅሱ ወገኖች የትላንቱም ህዝበ ውሳኔ ተመሳሳይ እንዳይሆን ስጋታቸውን ይገልጻሉ።

ግጨውን ከ10ዓመት በኋላ በብአዴን አማካኝነት ለትግራይ ክልል የተሰጠው ባለፈው ነሀሴ መጨረሻ ላይ በአዲስ ዓመት ዋዜማ መሆኑ ይታወሳል።

በሌላ በኩል ያለህዝብ ፍቃድ በህወሀት ፖለቲካዊ ውሳኔ በቅማንት አስተዳደር ስር እንዲሆኑ የተካለሉትን 42 ቀበሌዎች በተመለከተም ጥያቄ ተነስቷል።
የትላንቱ ህዝበ ውሳኔን ተከትሎ የተነሳው ጥያቄ እነዚህ 42 ቀበሌዎች ላይም ህዝበ ውሳኔ እንዲደረግ ነው።

የኢሳት የመረጃ ምንጮች እንደሚገልጹት ለቅማንት አስተዳደር እንዲኖር በህወሃት በኩል የብአዴንን እጅ በመጠምዘዝ 42ቱን ቀበሌዎች አካሏል።

ከትላንት ጀምሮ በአብዛኛው የሰሜን ጎንደር ህዝብ በሰፊው የተነሳው ጥያቄም ያለህዝብ ውሳኔ የተካለሉት ቀበሌዎችን ህዝብ ድምጽ እንዲሰጥበት ግፊት የሚያደርግ ነው።