የፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ አጽም በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ስላሴ ካቴድራል አረፈ

ኢሳት (ሰኔ 19 ፥ 2009)

በርካታ ወዳጅ ዘመዶቻቸው እንዲሁም አድናቂዎቻቸው በተገኙበት እሁድ ረፋድ ላይ በተካሄደው ስነ- ስርአት የተለያዩ ፖለቲካ ፓርቲ ድርጅት አመራሮች ታዋቂ ሰዎች መታደማቸውም ተመልክቷል።

የታዋቂው የህክምና ባለሙያ የመኢህድ መስራችና ፕሬዝዳንት የነበሩት የፕሮ/ር አስራት ወልደየስ መካነ- መቃብርና ሃውልት ላለፉት 18 አመታት ከነበረበት ባለወልድ ቤተክርስቲያን ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ እንዲነሳ መወሰኑ ቁጣ መቀስቀሱ ይታወቃል።

እሁድ ሰኔ 18/2009 ፍልሰተ አጽማቸው በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን ያረፈው ፕ/ር አስራት ወልደየስ የመአሕድ መስራችና ፕሬዝዳንት ነበሩ። አመጽ ለማነሳሳት ተንቀሳቅሰዋል በሚል በተመሰረተባቸው ክስ ወህኒ መውረዳቸውና እዚያው ሳሉ ባደረባቸው ህመም ከተዳከሙ በኋላ ለህክምና በሄደበት አሜሪካ ህይወታቸው ማለፉ ይታወሳል።

ፕ/ር አስራት ወልደየስ ከአባታቸው ከአቶ ወልደየስ አልታዬና ከእናታቸው ከወ/ሮ በሰልፉ ይዋሉ ጽጌ ሰኔ 12 ቀን 1920 አ/ም በአዲስ አበባ ከተማ መወለዳቸውን የህይወት ታሪካቸው ያስረዳል። በግብጽ ቪክቶሪያ የብሪታኒያ ኮሌጅ እንዲሁም በእንግሊዝ ኤድንብራ የህክምና ትምህርታቸውን የተከታተሉና የመጀምሪያው ኢትዮጵያዊ የቀዶ ህክምና ባለሙያ የሆኑት ፕ/ር አስራት ወልደየስ በሙያቸው ከፍተኛ አክብሮት አትርፈዋል።