የፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ሃውልት ሙሉ በሙሉ ፈረሰ

ኢሳት (ሰኔ 7 ፥ 2009)

የታዋቂው የህክምና ባለሙያ፣ የመአህድ መስራችና ፕሬዚደንት የነበሩት የፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ሃውልት ሙሉ በሙሉ ፈረሰ።

አፅማቸው ወዴት እንደሚወሰድ የታወቀ ነገር የለም። የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሃፊ አቡነ ሳዊሮስ ስለጉዳዩ እንደማያውቁ ለኢሳት ገልጸዋል።

ከሳምንታት በፊት የመካነ መቃብሩን አጥር በማፍረስ የተጀመረው እንቅስቃሴ ማክሰኞ ሰኔ 6 ፥ 2009 ሙሉ በሙሉ ሃውልቱን በማፍረስ ተጠናቋል። ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ፣ አጽማቸው ከመካነ መቃብር ያልወጣ ሲሆን፣ በቅርፅ የተሰራው ሃውልትም የተወሰደበት አልታወቀም። 

የፕ/ር አስራት ወልደየስ ሃውልትን መፍረስ ከሚቃወሙ ኢትዮጵያውያን አንዱ አቶ ሽመልስ ለገሰ ሁኔታውን በቁጣ ገልጸውታል።

ሃውልቱ ለምን እንደፈረሰ አልታወቀም። ሃውልቱን ለማፍረስ በደብሩ ሃላፊዎችም ሆነ በቤተ-ክህነት የተሰጠ ምክንያትም የለም።

የመላው አማራ ህዝብ ድርጅት መስራችና ፕሬዚደንት ፕ/ር አስራት ወልደየስ፣ በደብረብርሃን ከተማ አማሮችን ለአመጽ አነሳስተዋል የሚል ክስን ጨምሮ በርካታ ወንጀሎች ተዘርዝሮባቸው አመታትን በወህኒ አሳልፈው መሞታቸው ይታወቃል።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሃፊ የሆኑት አቡነ ሳዊሮስ ሃውልቱ ለምን እንደፈረሰ ከኢሳት ለቀረበላቸው ጥያቄ የሚያውቁት ነገር አለመኖሩን ገልጸዋል። ጉዳዩ የሚመለከተው ጠቅላይ ቤተክህነትን ነው በማለት ጥያቄውን ወደዚያ መርተዋል።

ሃውልቱ ለምን እንደፈረሰ ተወሰነ የሚለውን ለማጣራት ኢሳት ወደ ጠቅላይ ቤተክህነት እንዲሁም ወደ ባለወልድ ቤተክርስቲያን አስተዳደር ያደረገው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም።

ታዋቂው የህክምና ባለሙያና ፖለቲከኛ ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ በህክምና ሙያቸው እጅግ የተከበሩ ባለሙያ የነበሩ ሲሆን፣ የመላው አማራ ህዝብ ድርጅት (መአህድ)ን በመመስረት በህወሃት ኢህአዴግ የስልጣን ዘመን በአማሮች ላይ የተነጣጠረውን ጥቃት ለመመከት በመንቀሳቀሳቸውም ለረጅም ዓመታት በወህኒ ማሳለፋቸው ይታወቃል።

በቀድሞ ከርቸሌ ወህኒ ቤት ውስጥ በነበሩት ወቅት በገጠማቸው ከፍተኛ የጤና ችግር የውጭ ሃገር ህክምና እንዲያገኙ የተደረጉ ተማፅኖዎች በመንግስት በኩል ተቀባይነት ባለማግኘቱ ጤናቸው በከፍተኛ ሁኔታ ካሽቆለቆለ በኋላ ከሃገር እንዲወጡ ቢፈቅድም፣ ህይወታቸውን ማትረፍ አልተቻለም።

ፕ/ር አስራት ወልደየስ በ70 አመታቸው በአሜሪካ ፔንሲልቪኒያ ግዛት ፊላዴልፊያ ከተማ ግንቦት 6 ቀን 1991 ህይወታቸው አልፏል። የቀብራቸው ስነስርዓትም በትውልድ ሃገራቸው ኢትዮጵያ አዲስ አበባ ከተማ ባለወልድ ቤተክርስቲያን ተፈጽሟል። በቀብራቸው ስፍራ ላይ ለመታሰቢያ የቆመውም ሃውልድ ከ18 አመታት በኋላ እንዲፈርስ የተደረገ ሲሆን፣ አጽማቸው ወዴት እንደሚወሰድም አልታወቀም።