የድርቅ አደጋ በመባባሱ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ተጨማሪ ተረጂዎች ለምግብ ድጋፍ ተጋለጡ

ኢሳት (ሚያዚያ 16 ፥ 2009)

በኢትዮጵያ ተከስቶ ያለው የድርቅ አደጋ መባባስን ተከትሎ በኦሮሚያና የደቡብ ክልሎች ከአንድ ሚሊዮን በላይ ተጨማሪ ተረጂዎች ለምግብ ድጋፍ ተጋለጡ።

የመንግስት ባለስልጣናት የተረጂዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን በቅርቡ ይፋ ቢያደርጉም ቁጥሩን ግን ለህዝብ ከማሳወቅ ተቆጥበው ይገኛሉ።

ይሁንና በዚሁ የድርቅ አደጋ ዙሪያ አዲስ ሪፖርትን ያወጣው የተባበሩት መንግስታት የህጻናት መርጃ ድርጅት (ዩኒሴፍ) በቅርቡ በሁለቱ ክልሎች መጣል የነበረበት የበልግ ዝናብ በወቅቱ ባለፈው ባለመጣሉ ተጨማሪ ሰዎች ለምግብ ድጋፍ መጋለጣቸውን ይፋ አድርጓል።

በኦሮሚያ 1.1 ሚሊዮን ሰዎች እንዲሁም በደቡብ ክልል የተለያዩ ዞኖች ወደ 122ሺ አካባቢ ነዋሪዎች የምግብ ዕርዳታ ለመጠበቅ መገደዳቸውን ድርጅቱ አስታውቋል።

የቦረና፣ ምስራቅ ሃረርጌ፣ ጉጂ፣ ምዕራብ ጉጂ እንዲሁም የታችኛው የባሌ ዞን አካባቢ ያሉ 1.1 ሚሊዮን ሰዎች ለችግሩ በመጋለጣቸው ሳቢያ የዕርዳታ ምግብ እየቀረበላቸው መሆኑ ተመልክቷል።

የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና መንግስት ከወራት በፊት በጋራ ባቀረቡት ጥሪ 5.6 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ለአስቸኳይ የምግብ ድጋፍ እንደተጋለጡ ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል።

ይሁንና ለተረጂዎች የሚያስፈልገው የምግብ አቅርቦትና ድጋፍ በወቅቱ ባለመገኘቱ ምክንያት ችግሩ እየተባባሰ ከመሄዱ በተጨማሪ የተረጂዎች ቁጥር እየጨመረ እንዲሄድ አስተዋጽዖ ማድረጉን የእርዳታ ተቋማት ገልጸዋል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ባሰራጨው አዲስ ሪፖርት መሰረትም የተረጂዎች ቁጥር ወደ 7 ሚሊዮን አካባቢ መድረሱን ለመረዳት ተችሏል።

በሌሎች በድርቅ በተጎዱ አካባቢዎች ተመሳሳይ የተረጂዎች ቁጥር ይጨምራል የሚል ስጋት በመኖሩም ቁጥር ከሰባት ሚሊዮን ሊበልጥ እንደሚችል ተሰግቷል።

የተረጂዎች ቁጥር እያሻቀበ መሄዱ የእርዳታ አቅርቦቱ እንዲጨምር የሚያስገድድ መሆኑንም ዩኒሴፍ በሪፖርቱ አመልክቷል።

5.6 ሚሊዮን ለሚሆኑ የአስቸኳይ ጊዜ የምግብ ተረጂዎች ወደ አንድ ቢሊዮን ዶላር አካባቢ እንደሚያስፈልግ ሲገልፅ ቢቆይም የተረጂዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱ የሚፈለገውን የገንዘብ ድጋፍ ከፍ ያደርገዋል ተብሎ ይጠበቃል።

የአደጋ መከላከል ኮሚሽን ባለፈው ወር ባወጣው ሪፖርት በበርካታ አካባቢዎች የተረጂዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን አረጋግጦ ጉዳዩ ለሚመለከተው የመንግስት አካል መቅረቡን አስታውቋል።

ይሁንና የመንግስት ባለስልጣናት የተረጂዎችን አዲስ ቁጥር ይፋ ከማድረግ ተቆጥበዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለም የህጻናት መርጃ ድርጅቱ ከከፋ የምግብ እጥረት ጉዳት የተነሳ ወደ ማገገሚያ ጣቢያ የሚገቡ ህጻናት ቁጥር በየወሩ እየጨመረ በመሄድ ላይ መሆኑ ስጋት እንዳሳደረበት አክሎ ገልጿል።

ባለፈው ወር ወደ ማገገሚያ ጣቢያ የገቡ ህጻናት ቁጥሩ በ18 በመቶ ጭማሪን አሳይቶ በአሁኑ ወቅት 51 ሺ 184 ህጻናት ልዩ የህይወት የነፍስ አድን እንክብካቤ እየተደረገላቸው እንደሚገኝ ለመረዳት ተችሏል።