የዋጋ ንረት ያልተረጋጋው የግብርና ምርት ባለማደጉ መሆኑን የብሄራዊ ባንኩ ገዢ አመኑ

መጋቢት ፲፬ (አስራ አራት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የብሄራዊ ባንኩ ገዢ የሆኑት አቶ ተክለወልድ አጥናፉ ለፓርላማ አባላት እንደተናገሩት የዋጋ ንረቱን ለመቆጣጠር ባንኩ የተለያዩ ገንዘብ ነክ እርምጃዎችን ቢወስድም ሊሳካለት አልቻለም። ዋናው ችግር ከግብርና ምርት አቅርቦት ጋር የተያያዘ መሆኑን የገለጡት ገዢው፣ ግብርናው እስካላደገ ድረስ የዋጋ ንረትን መቆጣጠር እንደማይቻል ገልጠዋል። መንግስት በግብርና ምርቶች ላይ የሚታየውን የዋጋ ንረት ለመቆጣጠር አህል በብዛት ወደ አገር ውስጥ ለማስገባት መወሰኑን የገለጡት ገዢው ይህም ግን ዘላቂ መፍትሄ እንደማይሆን ገልጠዋል።

የኢትዮጵያ የንግድ ሚዛን ልዩነት 5 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን ያወሱት ገዢው በተለይ ወደ ውጭ የሚላከው የግብርና ምርት በመሆኑ ችግሩን አባብሶታል።

የብሄራዊ ባንክ ገዢው የሰጡት መግለጫ መንግስት እስከ ዛሬ ከሚለው ጋር የሚጋጭ ሆኗል። የመለስ መንግስት በተደጋጋሚ የስርጭት እንጅ የምርት እጥረት የለም በማለት የዋጋ ንረት መንስኤውን በነጋዴዎች ላይ ሲያሳብብ ቆይቷል። የኢኮኖሚ ባለሙያዎች የኑሮ ውድነቱ በአገሪቱ ውስጥ በቂ ምርት ባለመኖሩ የተፈጠረ ነው  በማለት ሲናገሩ ቢቆዩም መንግስት ግን ይህን ሀቅ ለመቀበል አሻፈረኝ ሲል ቆይቷል። ባለሙያዎች እንደሚሉት ደግሞ መንግስት የምርት እጥረት መኖሩን ካመነ 11 በመቶ የኢኮኖሚ እድገት እንዳገኘ ሌት ተቀን የሚለፍፈው ዜና ዋጋ ያጣበታል ።

የብሄራዊ ባንክ ገዢው ችግሩ የምርት እጥረት የፈጠረው መሆኑን በድፍረት መናገራቸው መናገራቸው፣ እውነታውን የተቀበሉ የመጀመሪያው የኢህአዴግ ባለስልጣን ያደርጋቸዋል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide