የወልቃይት ማንነት ጥያቄ ያነሱ 12 ግለሰቦች በሽብር ወንጀል ተከሰሱ

(ኢሳት ዜና–ሀምሌ 25/2009)የወልቃይት ማንነት ጥያቄ ያነሱ 12 ግለሰቦች በሽብር ወንጀል ተከሰሱ
ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ በክሱ ላይ የሽብር ቡድን አመራር መባላቸውን ጠበቆች ተቃውመዋል
ተከሳሾቹ ከጎቤ መልኬና ከኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ ጋር በመገናኘት ወልቃይት ውስጥ የሚገኙትን የመንግስት ደጋፊዎችና የትግራይ ተወላጆችን የሰፈራ ቦታ በመለየት ጥቃት ለመፈፀም ተንቀሳቅሰዋል የሚል ክስ ቀርቦባቸዋል፡፡
የወልቃይት አማራ ማንነት ጥያቄን ያነሱ 12ቱ ግለሰቦች ‹‹የወልቃይት አማራ ማንነት ጥያቄን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ከዞን እስከ ክልል ከዚያም አልፎ እስከ ፌዴሬሽን ጥረት ሲያደርጉ ነበር።
አሁን ግን ጥያቄያቸው ተግልብጦ በሽብር ወንጀል ተከሰዋል። ተከሳሾቹ የአርበኞች ግንቦት ሰባት አባል በመሆን በመደራጀትና የጦር መሳሪያ በመታጠቅ በሰው ህይወት እና ንብረት ላይ ጉዳት አድርሰዋል፥ የአካባቢው ነዋሪ ላይም ከባድ ስጋት ፈጥረዋል›› በሚል ተወንጅለዋል፡፡
ተከሳሾቹ ከጎቤ መልኬና ከኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ ጋር በመገናኘት ወልቃይት ውስጥ የሚገኙትን የመንግስት ደጋፊዎችና የትግራይ ተወላጆችን የሰፈራ ቦታ በመለየት ጥቃት ለመፈፀም ተንቀሳቅሰዋል የሚል ክስም ቀርቦባቸዋል፡፡
ተከሳሾቹ በተለይ ከኮሌኔል ደመቀ ዘውዱ ጋር በመገናኘት የወልቃይት አማራ የማንነት ጥያቄን ለመመለስ የመንግስት ደጋፊዎች ላይ እርምጃ መውሰድ እንዳለባቸው ተልዕኮ ወስደዋል በሚልም ተፈርጀዋል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በአርማጭሆና ወልቃይት ከሚገኙ የግንቦት ሰባት ታጣቂዎች፣ እንዲሁም በክሱ የግንቦት 7 አመራር ነበር ከተባለው ጎቤ መልኬ ከሚመራቸው 80 ያህል ታጣዊዎች ጋር ጫካ ገብተዋል ይላል በሕወሀት ኣአቃቤ ሕግ የቀረበባቸው የክስ ሰነድ።
ወልቃይት ውስጥ በነበረ የመንግስት ጦር ላይ ጥቃት በመፈፀም፣ የትግራይ ተወላጆችና ባለሀብቶች የሰፈራ መኖሪያ ካምፖች ላይ ጥቃት አድርሰዋልም ነው የተባሉት፡፡
ከተከሳሾቹ መካከል አብዛኛዎቹ ወልቃይት ውስጥ የሚኖሩ ሲሆኑ መኖሪያቸው ሰ/ጎንደር ጠገዴ ወረዳ የሆኑ ሁለት ተከሳሾች ‹‹እኛንም የወልቃይት ጥያቄ ይመለከተናል›› ብለው አብረው ሲንቀሳቀሱ እንደነበር በክሱ ላይ ተጠቅሷል፡፡
በሌላ በኩል የኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ ጠበቃ የደንበኛቸው ጉዳይ በሌላ ፍርድ ቤት እየታየ ባለበት ሁኔታ በዚህ ክስ ‹‹የሽብር ቡድን አመራር›› ተብለው መጠቀሳቸው የኮሎኔሉን በህግ ፊት ንፁህ ሆኖ የመታየት መብት የነፈገ መሆኑን በመግለፅ ተቃውሞ አቅርበዋል፡፡ በሌሎች ክሶች ላይም ኮሎኔሉ በተመሳሳይ ሁኔታ የተጠቀሱ ሲሆን ፍርድ ቤቱ ጠበቆቹ አቤቱታቸውን በክስ መቃወሚያ ማቅረብ እንደሚችሉ አሳውቋል፡፡