የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻነት ግንባት (ኦብነግ) እና አርበኞች ግንቦት 7 በጋራ ለመስራት ስምምነት ተፈራረሙ

ኢሳት (ግንቦት 10 ፥ 2009)

የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻነት ግንባት (ኦብነግ) እና አርበኞች ግንቦት 7 በጋራ ለመስራት ተስማሙ። በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ እየደረሰ ያለውን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮች በጋራ ለመታገልና ከሌሎች የኢትዮጵያ የለውጥ ሃይላት ጋር ለመተባበር መስማማታቸውን ድርጅቶቹ ጀርመን ፍራንክፈርት ባወጡት የጋራ መግለጫ አስታውቀዋል። 

የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻነት ግንባር (ኦብነግ) እና አርበኞች ግንቦት 7 እኤአ ከሜይ 15 እስከ ሜይ 17 በጀርመን ፍራንክፈርት ለሶስት ቀናት ተወያይተው የኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ በጥልቀት መገምገማቸውን ባወጡት የጋራ መግለጫ አስታውቀዋል።

ስልጣን ላይ ያለው የህወሃት ኢህአዴግ አገዛዝ በሃገሪቱ ከፍተኛ ቀውስ ፈጥሯል በማለት በጋራ መግለጫቸው ያወጡት ሁለቱ ድርጅቶች፣ ይህ አስጊ ሁኔታ በፍጥነት ካልተቀለበሰ ሰብዓዊና ፖለቲካዊ ቀውስ በኢትዮጵያና በአካባቢው እንደሚፈጠር ያላቸውንም ስጋት ገልጸዋል። ይህንን ስጋት ለማስወገድ በጥልቀት መምከራቸውንና በጋራ ለመታገል መወሰናቸውንም አስታውቀዋል።

የህወሃት/ኢህአዴግ አገዛዝ እንዲወገድና የኢትዮጵያ ህዝብ ሰቆቃ እንዲያበቃል በግንባር ቀደምትነት መሰለፋቸውን የገለጹት ኦብነግና አርበኞች ግንቦት 7 ለሌሎች የዴሞክራሲ ሃይሎችም ጥሪ አቅርበዋል። ተመጣጣኝ ውክልና ወደ አለበት ሃቀኛ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለመሸጋገር የሚያስችሉ መሰረቶችን በጋራ መኖራቸውንም በመግለጫቸው ፈንጥቀዋል።

የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻነት ግንባር  ኦብነግ ሊቀመንበር የሆኑት መሃመድ ኦማር ኡስማን እና የአርበኞች ግንቦት 7 ሊቀመንበር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ጀርመን ፍራንክፈርት ረቡዕ ግንቦት 9 ፥ 2009 እኤአ ሜይ 17 ፥ 2017 የተፈረራረሙት የትብብር ሰነድ ተከትሎ የወጣው የጋራ መግለጫ ለአለም አቀፉ ማህበረሰብም ጥሪ አቅርቧል።

የኢትዮጵያ የጦርና የፖሊስ ሰራዊት አባላት እንዲሁም የደህንነቱ ተቋም ሰራተኞች ህዝብን ከመፍጀትና ከማሰቃየት እንዲታቀቡ ያሳሰበው የሁለቱ ኢትዮጵያውያን ድርጅቶች የጋር መግለጫ ይልቁንም ከህዝብ ጎን እንዲሰለፉና ለለውጥ የበኩላቸው አስተዋጽድዖ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል።