የኢኮኖሚ እድገቱ በምርታማነትና በኢትዮጵያ ሀብት ላይ የተመሰረተ ሳይሆን፤ በአገልግሎት ሰጪ ዘርፍ በኩል እንደሆነ ተገለጸ

ጥቅምት ፪ (ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:- መንግስት የአገሪቱ ኢኮኖሚ ለ10ኛ አመት በድርብ ቁጥር ያድጋል ቢልም፤ የኢኮኖሚ እድገቱ በምርታማነትና በኢትዮጵያ ሀብት ላይ የተመሰረተ ሳይሆን፤ በአገልግሎት ሰጪ ዘርፍ በኩል እንደሆነ ተገለጸ

“ዚስ ኢዝ አፈሪካ” የተሰኘው የተሰኘው ድረገጽ እንደዘገበው፤ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በዓለም ላይ በፍጥነት ከሚያድጉት አምስት ኢኮኖሚዎች ውስጥ ነው ቢባልም፤ የቴሌኮሚኒኬሽን አገልግሎት፤ የቴክኖሎጂ ዘርፍና፤ የባንኩ ዘርፍ በጣም  ሁዋላቀርና በአፍሪካ ደረጃ እንኩዋን ከአማካኝ በታች እንደሆነ ተመልክቷል።

የቴሌኮሚኒኬሽን ተቋም በመንግስት በብቸኝነት መያዙ፤ በመንግስት የተከለከሉ ነገሮች መብዛታቸው፤ የኢንተርኔት ግንኙነቱ ደካማና ዘገምተኛ መሆን፤ ካሉት የንግድና የገንዘብ ተቋማት 40 ከመቶው በአዲስ አበባ ብቻ መከመራቸው፤ አለ የተባለውን እድገት የተዛባ እንዳደረጉት ዜናው ያትታል።

በባንኩ ዘርፍ የውጭ አልሚዎች ወይንም መዋእለ ንዋይ ፍሰት መከልከላቸውም እንደተጨማሪ ችግር ተጠቅሷል።

አሁንም ከ45 በመቶ በላይ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በግብርና ላይ የተመሰረተ ሲሆን፤ 80 ከመቶ የሚሆነው የኢትዮጵያ ሀይል በስራ የተሰማራው በግብርና ዘርፍ መሆኑ ይታወቃል።

ዚስ ኢዝ አፍሪካ ድረገጽ ኢትዮጵያ እንደጎረቤቷ ኬንያ በቴክኖሎጂ ዝግጁነትና በገንዘብ ዝውውር ረገድ ወደፊት አልንዳልሄደች ዘገባው ያመለከተ ሲሆን፤ ከብዙ የአፍሪካ አገሮች አንሳ አንሳ ተገንታለች ሲል ዘግቧል።

በኢትዮጰያ አለ የሚባለው እድገትም በምርታማነትና በአገሪቱ የተፈጥሮ ሀብት ላይ ሳይሆን በአገልግሎት ዘርፉ ላይ እንደተሰመረተ ተንገሯል።