የኢትዮጵያ ቱሪዝም አባት በመባል የሚታወቁት አቶ ሐብተስላሴ ታፈሰ ከዚህ አለም በሞት ተለዩ

(ኢሳት ዜና–ነሀሴ 3/2009)የኢትዮጵያ ቱሪዝም አባት በመባል የሚታወቁት አቶ ሐብተስላሴ ታፈሰ በ90 አመታቸው ከዚህ አለም በሞት ተለዩ።
ለረጅም አመታት የኢትዮጵያ ቱሪዝም መለያ ምልክት የሆነውን “የ13 ወር ጸጋ ፈጣሪ” የሆኑት አቶ ሀብተስላሴ ታፈሰ ህይወታቸው ያለፈው በባልቻ ሆስፒታል ህክምናቸውን በመከታተል ላይ በነበሩበት ወቅት መሆኑ ታውቋል።
የኢትዮጵያ የቱሪዝም አባት የሚባሉት አቶ ሀብተስላሴ ታፈሰ በቱሪዝም ኮሚሽነርነትና የቱሪዝም አስጎብኝ በመሆን የኢትዮጵያን ታሪካዊ ቅርሶችና ባህላዊ እሴቶችን በማስተዋወቅ የዜግነት ግዴታቸውን ተወጥተዋል።
የኢትዮጵያ ታሪካዊ ቅርሶች በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣የሳይንስና የባህል ድርጅት(ዩኔስኮ)እንዲመዘገቡና እውቅና እንዲያገኙ አድርገዋል።
ለኢትዮጵያ የቱሪዝም እድገት ላደረጉት አስተዋጽኦ በተለያዩ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የእውቅና ሽልማት አግኝተዋል።
የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥንና ሬዲዮ በኢትዮጵያ የቱሪዝም አባት ሞት የተሰማውን ሐዘን እየገለጸ ለመላው ቤተሰቦቻቸው፣ወዳጆቻቸውና ለኢትዮጵያ ህዝብ መጽናናትን ይመኛል።