የኢትዮጵያ መንግስት የኢንተርኔት አፈናውን መቀጠሉን ሪፖርተርስ ዊዝ አውት ቦርደርስ አስታወቀ

ሰኔ ፪ (ሁለት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ድርጅቱ እንደገለጠው የኢትዮጵያ መንግስት የኢንትርኔት ተጠቃሚዎች ስማቸውን ሳይገልጡ የሚጠቀሙበትን እና እንዳይታዩ የታገዱ ድረገጾችን ለማየት የሚጠቅመውን ቶር ኔት ወርክ ዘግቷል።

ሪፖርተርስ ዊዝ አውት ቦርደርስ  ማተሚያ ቤቶች አዲስ ያወጡትን ቅድመ ምርምራን የሚያጠናክረውን ውልም ተችቶአል።

ፓርላማው በቅርቡ አዲስ የወጣውን የቴሌኮሚኒኬሽን ህግ ማጽደቁ ይታወሳል።

በአዲሱ ህግ ከየቴሌኮሚኒኬሸን መሳሪያዎች ጋር የተያያዙ ወንጀሎች  ከ10-15 ዓመታት በሚደርስ ጽኑ እሥራትና ከ100ሺ እስከ 150ሺ ብር የሚደርስ የገንዘብ መቀጮ የሚያስቀጣ ነው ተደንግጓል፡፡

የቴሌኮሚኒኬሸን አገልግሎት ከመስጠት ወንጀል ጋር ማለትም ሕጋዊ ንግድ ፈቃድ ሳይኖር የቴሌኮሚኒኬሸን አገልግሎት መስጠትም  ቅጣት ከሚያስከትሉት አንዱ መሆኑን ረቂቅ አዋጁ ያትታል።

የቴሌኮም ማጭበርበር ተግባር ህገወጥ መሳሪያ በመጠቀም ወይም ህገወጥ የቴሌኮም አገልግሎት በመስጠት ብቻ ሳይሆን ህጋዊ መሳሪያዎችንና አገልግሎቶችን በመጠቀምም ሊፈጸም እንደሚችል የሚያትተው ይኽው ረቂቅ አዋጅ በአጥፊዎች ላይ ከ3-8 ዓመታት እሥራትና ከብር 30ሺ እስከ 80ሺ  የሚደርስ መቀጮ ይደነግጋል፡፡

የቴሌኮሚኒኬሸን አገልግሎት ዋጋና ታሪፍ ማጭበርበርም እንዲሁ ቅጣትን የሚያስከትል ነው፤ ወንጀሉም  ከ5-10 ዓመታት የሚደርስ ጽኑ እሥራትና አገልግሎት ሰጪ ድርጅቱ የደረሰበትን ኪሳራ ሶስት እጥፍ የገንዘብ መቀጮ የሚያስቀጣ ሆኖ ተደንግጓል፡፡

በዚህ የወንጀል ድርጊት የተከሰሰም ከ10-20 ዓመታት እሥራትና በዚሁ ሕገወጥ አገልግሎት የተገኘው ገቢ እስከ አሥር እጥፍ የሚደርስ መቀጮ የሚያሰቀጣ ሲሆን የዚህ ሕገወጥ አገልግሎት ተጠቃሚዎች ደግሞ ከሶስት ወራት እስከ ሁለት ዓመት እስራትና ከ2 ሸ500 ብር እስከ 20ሺብር መቀጮን ይጥላል፡፡

የኮልባክ አገልግሎትን የሚመለከቱ ወንጀሎች ማለትም የሃገር ውስጥ የቴሌኮሚኒኬሸን ድርጅት ሳያውቀው የሌላን ሃገር የቴሌኮሚኒኬሸን ድርጅት የጥሪ ቶንን ለዓለምአቀፍ ግንኙነት መጠቀም ከ3 ወራት እስከ 2 ዓመታት እሥራትና ከብር 2 ሺ500 እስከ 20 ሺ ብር መቀጮ የሚያስቀጣ ሆኖ በረቂቅ አዋጁ ተደንግጓል፡፡

ረቂቅ አዋጁ ሌሎች ወንጀሎች ሲል የገለጻቸው ማለትም ሲም ካርድ፣የደንበኞች መለያ ቁጥር ወይንም ኮድ እና ሌሎች የቴሌኮሚኒኬሸን መሳሪያዎችን በህገወጥ መንገድ ማባዛት፣አስመስሎ መሥራት እንዲሁም በማናቸውም ዓይነት ወይም በሌላ ማናኛውም መንገድ በመጠቀም በሕዝብ ቴሌፎን አማካይነት ሊገኝ የማይችልን  አገልግሎት ለማግኘት የሚያስችል ማንኛውም ሕገወጥ ድርጊት መፈጸም ከባድ ቅጣትን እንደሚያሰከትል ደንግጓል፡፡  የኢትዮጵያን መንግስት መልካም ምስል በኢንተርኔት በሚያበላሹት ላይም ቅጣት ይጣልባቸዋል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide