የአንድነት ፓርቲ ልሳን “ፍኖተ ነፃነት” ጋዜጣ በአገሪቱ በየትኛውም ማተሚያ ቤት እንዳትታም ታገደች

ህዳር ፲፭ (አስራ አምስት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ከአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ  ጽህፈት ቤት የወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው ህትመቷ ከታገደ በሁዋላ በቅርቡ ዳግም መታተም የጀመረችው ፍኖተ-ነፃነት  ከእንግዲህ በ አገሪቱ በሚገኝ በየትኛውም ማተሚያ ቤት እንዳትታተም  እገዳ ተጥሎባታል።

ፓርቲው በወቅቱ አገራዊ ፖለቲካ ዙሪያ ነገ ህዝባዊ ስብሰባ የሚያካሂድ ሲሆን፤ በድርጅቲ ልሳን ላይ ስለተጣለው አዲስ እገዳ አስመልክቶ በስብሰባው ማብራሪያ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል።

በዋናነት የነገው ስብሰባ የተጠራው  በአገሪቱ ስለሚታየው  እጅግ  አሣሳቢ የሆነ የፖለቲካ ሁኔታ ዙሪያ ለህብረተሰቡ ለማሳወቅና በመፍትሔ አቅጣጫዎች ዙሪያ ለመነጋገር እንደሆነ የፖርቲው ሊቀ-መንበር ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ ተናግረዋል።

ህዝቡ እየደረሰበት ያለውን በደልና የኑሮ ውድነቱን ተሸክሞ እያጉረመረመ ከመኖር በዘለለ አንዳችም ትርጉም ያለው ንቅናቄ ሲያደርግ አለመታየቱን የተናገሩት ዶ/ር ነጋሶ፤ በዚህ በኩል የእስልምና እምነት ተከታዮች እያካሄዱት ያለው ንቅናቄ የተሻለ ነው ማለታቸውን የ አዲስ አድማስ ዘገባ ያመለክታል።
የገዥውን ፓርቲ ጨምሮ በ አገሪቱ ውስጥ ስላሉ የተቃዋሚ ፓርቲዎች እንቅስቃሴ አስመልክቶም ውይይት እንደሚደረግ ዶክተር ነጋሶ ጠቁመዋል።

 

በዚህ ዙሪያ ለነገው ስብሰባ በእርሳቸው የተዘጋጀው የውይይት መነሻ ሃሳብ፤ በኢትዮጵያ  መድብለ ፓርቲ አለመኖሩን፣ ዲሞክራሲያዊ ያልሆነና አፋኝ ገዥ ፓርቲ መኖሩን፣ ገዥው ፓርቲ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትን የማይከተልና አፋኝ ሥርዓት መሆኑን፤ እንዲሁም ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ጥንካሬና ጽናት የሚጐድላቸውና የተበጣጠሱ እንደሆኑ የሚያመለክት ነው።

 

በሌላ ዜና ደግሞ ዓመታዊ የግብር ግዴታውን ባለመወጣቱ ምክንያት የቀረበበትን ክስ ተከትሎ ላለፉት ሶስት ወራት ከሕትመት ውጪ ለመሆን የተገደደው “ኢትዮ ቻናል” ጋዜጣ በዛሬው ዕለት በድጋሚ ወደ ሕትመት ለመመለስ ቢዘጋጅም የብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት ፈቃደኛ ባለመሆኑ ለመታተም ሳይችል ቀርቷል፡፡
የኢትዮ ቻናል ጋዜጣ ባለቤቶች አቶ ሳምሶን ማሞ እና ባለቤቱ ወ/ሮ ዘውድነሽ ታደሰ በሐምሌ ወር 2004 ዓ.ም
ከግብር ጋር በተያያዘ በቀረረበባቸው ክስ ታስረው በዋስ ተለቀዋል፡፡

የኢህአዴግ ደጋፊ መሆኑን በአደባባይ የሚናገረው አቶ ሳምሶን በእስሩ ክፉኛ በመበሳጨት “ኢህአዴግን መደገፍ ምን ዋጋ አለው” እያለ ሲናገር በተደጋጋሚ ተደምጧል፡፡

የቀረበበት ክስ የግብር ጉዳይን ሰበብ በማድረግ ሆን ተብሎ እሱን
ለመጉዳት የሚያስቡ ወገኖች የጠነሰሱት መሆኑን እና የእሱ ግብር አለመክፈል ለመንግስት አሳሳቢ ነገር አለመሆኑን
በተደጋጋሚ ለጋዜጦች መግለጫ በመስጠት ተቃውሞን ገልጾአል፡፡
በሀገሪቱ ህግ መሰረት አንድ ግብር ባለመክፈል የተከሰሰ ሰው ሁለት ዓመት ሳይሞላው በዚያው ፈቃድ መልሶ ስራ ውስጥ መግባት
የማይፈቀድ ቢሆንም አቶ ሳምሶን ግን በልዩ ሁኔታ ከሕግ ውጪ ተፈቅዶለት፣የቀረበበት ክስም ተሰርዞለት በቀድሞ
ስሙ ወደ ስራ እንዲመለስ መደረጉ ብዙዎችን ያነጋገረና ያስገረመ፣ የህግ ስርዓቱም የቱን ያህል እየሻገተ መምጣቱን
ያሳየ እንደነበር ጉዳዩን በቅርብ የተከታተሉ ተናግረዋል፡፡
አቶ ሳምሶን በዚህ መልኩ ውለታ ተደርጎለት ከቅዳሜ ህዳር 15 ቀን 2005 ኣ.ም ጀምሮ ወደገበያ ለመመለስ
ማስታወቂያ አስነግሮ የነበረ ቢሆንም ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት “ወረቀት የለኝም” በሚል ሰበብ ሕትመቱን
ተቀብሎ ለማተም ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቷል፡፡

አቶ ሳምሶን ከሕግ ተጠያቂነት ነጻ እንዲወጣ የረዱትን ባለስልጣናት
በተለመደ መልኩ ተማልዶ ጋዜጣውን የመቀጠሉ ጉዳይ የማይቀር እንደሆነ  መነገሩን  ምንጫችን ዘግቧል፡፡