የአቶ አሰፋ ጫቦ የቀብር ስነስርዓት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ስላሴ ካቴድራል ተፈጸመ

ኢሳት (ሚያዚያ 27 ፥ 2009)

የታዋቂው የህግ ባልሙያ፣ ፖለቲከኛና ጸሃፊ አቶ አሰፋ ጫቦ የቀብር ስነስርዓት ሚያዚያ 2009 አም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ስላሴ ካቴድራል ተፈጸመ።

ለ25 አመታት በአሜሪካ ስደት ላይ የነበሩት አቶ አሰፋ ጫቦ በሚኖሩበት ዳለስ ቴክሳስ ግዛት በ75 አመታቸው በቅርቡ ከዚህ አለም በሞት መለየታቸው ይታወሳል።

አቶ አሰፋ ጫቦ የኢትዮጵያ ጭቁን አብዮታዊ ትብብር (ኢጭአት) ፓርቲ መስራችና ሊቀመንበር በመሆን በደርግ ጊዜ የታወቁ ፖለቲከኛ ነበሩ። ከዚያም በኋላ በሽግግሩ መንግስት ወቅት የኦሞ ህዝቦች በመወከል የምክር ቤት አባል ሆነው ሲንቀሳቀሱ ነበር።

በኋላም በአገዛዙ ተፅዕኖ ከሃገር ተሰደው ላለፉት 25 አመታት በአሜሪካ የተለያዩ ግዛቶች ኖረዋል።

አቶ አሰፋ ጫቦ ታዋቂ ብዕረኛና ሃገራቸውን እጅግ የሚወዱ ሰው ነበሩ። በኋላ “የትዝታ ፈለግ” የተሰኘ መጽሃፍ አሳትመው ቀደምት ስራዎቻቸውን ለህዝብ አቅርበዋል።

የአቶ አሰፋ ጫቦ አስከሬን  ወደ አዲስ አበባ  ተጉዞ ወዳጅ ዘመድና አድናቂዎቻቸው በተገኙበት ሰነስርዓት ቀብራቸው በቅድስ ስላሴ ቤተክርስቲያን አርብ ሚያዚያ 27 ፥ 2009 በ 6 ሰዓት ተፈጽሟል።

አቶ አሰፋ ጫቦ የአራት ልጆች አባትና የዘጠኝ ልጆች አያት ነበሩ።