የአቶ አሰፋ ጫቦ ቀብር የሰነ-ስርዓት በቅድስት ስላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም ታወቀ

ኢሳት (ሚያዚያ 24 ፥ 2009)

የአቶ አሰፋ ጫቦ የቀብር ስነስርዓት የፊታችን አርብ በአዲስ አበባ ቅድስ ስላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም ታወቀ። አስከሬኑ ማክሰኞ ከዳላስ አሜሪካ የተነሳ ሲሆን፣ ሃሙስ ከሰዓት አዲስ አበባ እንደሚደርስም ከወጣው መርሃ ግብር መረዳት ተችሏል።

ሚያዚያ 5 ቀን 2009 አም በ73 አመታቸው በዩ ኤስ አሜሪካ ቴክሳስ ግዛት ዳለስ ከተማ ያረፉት አቶ አሰፋ ጫቦ፣ ቅዳሜ ሚያዚያ 21 ፥ 2009 በዳለስ ቅዱስ ሚካዔል ቤተክርስቲያን ወዳጆቻቸውና ዘመዶቻቸው በተገኙበት ጸሎተ ፍትሃት ተደርጎላቸዋል። በስነስርዓቱ ላይ ከዋሽንግተን ዲሲና ከተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች የተጓዙ ወዳጆቻቸው መገኘታቸውም ታውቋል።

የጸሃፊው፣ የህግ ባለሙያውና የፖለቲከኛው የአቶ አሰፋ ጫቦ አስከሬን፣ ማክሰኞ ዕለት በዩናትድ አረብ ኤመሬት አውሮፕላን ዳለስ ቴክሳስ የተነሳ ሲሆን፣ ሃሙስ ከሰዓት አዲስ አበባ ቦሌ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ እንደሚደርስም መረዳት ተችሏል።

የቀብር ስነስርዓቱ አርብ ሚያዚያ 27 ፥ 2009 አም በአዲስ አበባ ቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን እንደሚፈጸም ከወጣው መርሃ ግብር መረዳት ተችሏል።