የአቶ ስብሀት ነጋ የሰጡት አስተያየት አነጋጋሪ ሆኗል

የካቲት 20 ቀን 2004 ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-አቶ ስብሀት እርሳቸው የሚመሩት የሰላምና አለማቀፍ ተቋም ኢንሰቲቲዩት ባዘጋጀው ውይይት ላይ ነው፣ ጸረ ሙስና ኮሚሽን ለምን በጥቃቅን የሙስና አይነቶች ላይ ብቻ ያተኩራል በማለት ጠይቀው፣ በኢትዮጵያ ሙስናን ለማጥፋት ፍላጎት እንጅ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ብሎ ነገር የለም። ይህ በሌለበት ተግባርም ውጤትም አይኖርም። ቁርጠኛ ሌባ አለ ቁርጠኛ ተዋጊ ግን የለም።” በማለት እርሳቸው በአምሳያቸው የቀረጹትን የመለስን መንግስት ነቅፈዋል።
አቶ ስብሀት ከፍተኛ በሆኑ የፖለቲካ አመራሮች ላይ በሙስና እንደተዘፈቁ ወሬ ይሰማል፣ ለምን ድነው ፍተሻ የማይደረገው በማለት ጠይቀዋል።

ሀይማኖት ሙስናን አያጠፋም ፣ በሀይማኖት አካባቢ የምንሰማው ስንት ጉድ አለ፣ ትልቁ ሙስና ያለው እዛ ነው በማለትም አክለዋል።

የአቶ ስብሀት ንግግር ከአቶ መለስ ጋር ያላቸው ልዩነት እየሰፋ መምጣቱን አመላካች ነው በማለት ሁለት የቀድሞ የህወሀት አባላት መናገራቸውን ዘገባያችን የላከው ሪፖርት ያመለክታል። በንግግራቸው ውስጥ ወ/ሮ አዜብና አቶ መለስ ይጠየቁ ብለው በስም መናገር ነው እንጅ የቀራቸው፣ የሙስና ምርመራው ከእነሱ መጀመር እንዳለበት ፍንጭ ሰጥተዋል ያሉት አባሎቹ፣  አቶ ስብሀት ከኢፈርት ስራ አስኪያጅነት በወ/ሮ አዜብ መስፍን አማካኝነት ከሀላፊነት ከተባረሩበት ጊዜ ጀምሮ በሁለቱ ሰዎች መካከል እየሰፋ የመጣው ልዩነት በገሀድ ታይቷል ብለዋል።

አቶ ስብሀት የአቶ መለስ ጠባቂ ተደርገው የሚታዩትን አቡነ ጳውሎስን ከወራት በፊት ከተቹ በሁዋላ፣ አሁንም በድጋሜ መተቸታቸው ግለሰቡ ሁሉን ነገር በተቆጣጠረው የመለስ አገዛዝ እና የአገዛዙ አስጠባቂዎች ላይ ያላቸውን የተመናመነ ተስፋ የሚያመልክት ነው ተብሎአል።

ነባሩ ታጋይ ህወሀት ወደ አንድ ሰው አመራር እየተሸጋገረ ነው የሚለው ወቀሳ እንደሚያሳስባቸው፣ አውራ ፓርቲ የሚባለውን ነገር እንደማያውቁ መግለጣቸው መዘገቡ ይታወሳል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide