የአትሌት ፈይሳ ሌሊሳ ቤተሰቦች መንግስት ለደህንነቱ የሰጠው ማስተማመኛ ተዓማኒነት የለውም አሉ

ኢሳት (ነሃሴ 19 ፥ 2008)

ሰሞኑን በሪዮ ኦሎምፒክ በመንግስት ላይ ተቃውሞን ያቀረበ የአትሌት ፈይሳ ሌሊሳ ቤተሰቦች መንግስት ለደህንነቱ የሰጠው ማስተማመኛ የማይታመን ነው በማለት አትሌቱ የወሰደውን እርምጃ በይፋ ደገፉ።

በወጣቱ ውሳኔ ዙሪያ ከሮይተርስ የዜና አውታር ጋር ቃለምልልስን ያደረጉ የአትሌት ፈይሳ ወላጅ እናት ልጃቸው የወሰደውን ዕርምጃ ተገቢ እንደሆነ በመግለጽ ልጃቸው ባለበት ሃገር እንዲቀር አሳስበዋል።

አትሌት ለሊሳ ፈይሳ በሃገር ቤት በነበረው ቆይታው በሃገር ውስጥ በሚካሄዱ ግድያዎችና ዕስራት እጅጉን ሲያዝን መሰንበቱን ወላጅ እናቱ ለሊና አውታሩ አስረድተዋል።

የደስታ ገጽታ እየታየባቸው ከአትሌቱ ባለቤት እና ልጆቹ ጋር ያላቸውን አስተያየት የሰጡት የአትሌት ፈይሳ ሌሊሳ ወላጅ እናት፣ “መንግስት የሚለው ነገር የሚታመን ነው ወይ?” ሲሉ ለመንግስት ከደህንነቱ የቀረበን ዋስትናን በማስመልከት ጥያቄን አቅርበዋል።

“እኔ ግን እምነት የለኝም” ሲሉ ምላሽን የሰጡት የአትሌቱ እናት፣ ልጃቸው ባለበት ሃገር ሰላም እንዲሆንላቸው መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

የአትሌት ፈይሳ ሌሊሳ ባለቤት በበኩላ ባለቤቷ በወሰደው እርምጃ መገረም እንዳልተፈጠረባትና አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ በተለያዩ መገኛኛ ብዙሃንና ድረገጾችን በሚያያቸው አሳዛኝ ግድያዎችና አፈና ውስጡ ይነድ ነበር በማለት ባለቤቷ ያላትን አጋርነት ገልጻለች።

በአለም አቀፍ መገኛኛ ብዙሃን ዘንድ አሁንም ድረስ መነጋገሪያ ሆኖ የሚገኘው አትሌት ፈይሳ በሪዮ ኦሎምፒክ የማራቶን ድሉ ወቅት እጆቹን ከጭንቅላቱ በላይ በማጣመር በሃገሪቱ እየተፈጸመ ያለውን ግድያ ማውገዙ ይታወሳል።

አትሌቱ የወሰደውን እርምጃ ተከትሎ በርካታ አለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ሰፊ ሽፋንን በመስጠት በኢትዮጵያ ያለውን የፖለቲካ ሁኔታ በዋቢነት በማስደገፍ ሰፊ ዘገባን እያቀረቡ ይገኛል።

ነዋሪነታቸው በተለያዩ የአለማችን ሃገራት የሆነ ኢትዮጵያውያን አትሌቱ የወሰደውን እርምጃ በመደገፍ ባለፉት ጥቂት ቀናቶች ከ137ሺ ዶላር በላይ ገንዘብ መሰብሰቡን ከአዘጋጆቹ ለመረዳት ተችሏል።

አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ በሪዮፕ ኦሎምፒክ የወሰደው እርምጃ ቅድመ ዝግጅት የተደረገበት እንደነበር በመግለጽ ከእንግዲህ ወዲያ ቢሞትም እንደማይቆጨው ከኢሳት ጋር ባደረገው ቃለምልልስ መግለጹ የሚታወስ ነው።