የታዋቂው ገጣሚ ሻለቃ ክፍሌ አቦቸር አራተኛው የስነ-ግጥም መጽሃፉ ተመረቀ

ኢሳት (ሰኔ 19 ፥ 2009)

“ሚስጥሯን-ያልገለጠልን” በሚል ርእስ በ175 ገጽ እና 61 የግጥም መድብሎችን የያዘው የስነ-ግጥም መጽሃፍ ቅዳሜ ሰኔ 24 ቀን 2017 በቨርጂኒያ አርሊንግተን የተመረቀ ሲሆን በዝግጅቱ ላይ የደራሲው ወዳጆችና አድናቂዎች እንዲሁም በኪነ-ጥበብ ዘርፍ ታዋቂ ኢትዮጵያውያን ተገኝተዋል። 

በምረቃው ዝግጅት ላይ “ትላንትን ማስታወስ፣ ነገን ማሰብ ካልተቻለ የዛሬ ፈተና አይተላለፍም” በማለት የእንኳን ደህና መጣችሁ የመግቢያ ንግግር ያደረገው የመጽሃፉ ደራሲ ሻለቃ ክፍሌ አቦቸር ለሀገረ- ኢትዮጵያ ክብር “ሀገሬ” ላሏት የሀገር ፍቅር ሲሉ የአካል ፈተናና የህይወት መስዋእትነት ለከፈሉ ዛሬም እንደ ትላንቱ ለኢትዮጵያ ሉአላዊነት፣ ሰንደቅ አላማ፣ ለዜጎች መብትና ነጻነት ለሚሟገቱ ለኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች ይሄ መጽሃፍ የጽናታቸው መሰረት እንዲሆን ፍላጎታቸውን ገልጸዋል።

በተያያዘ ዜና በካናዳ ቶሮንቶ በተዘጋጀ ስነ-ስርአት የተወሰኑ የምክር ቤት አባላት ለድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ሽልማት ሰጥተዋል። በእለቱ በካናዳ የኢትዮጵያውያን ማህበር የቤተሰብ ምሽት በማዘጋጀት ለድምጻዊው የክብር ሽልማት መስጠታቸው ታውቋል።