የቦረናና ጉጂ ዞን ነዋሪዎች ድረሱልን ይላሉ

መጋቢት ፲፬ (አስራ አራት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ነዋሪዎቹ ጥሪውን ያሰሙት የሼክ ሙሀመድ ሁሴን አላሙዲን የወርቅ ኩባንያ የሆነው ሚድሮክ ወርቅ ፣ ለተጨማሪ ወርቅ ፍለጋ አካባቢውን ይፈልገዋል ተብሎ መነገሩን ተከትሎ ነው።

የኢሳት ምንጮች እንደገለጡት ከአመት በፊት በአካባቢው ተነስቶ የነበረው ተቃውሞ የመጨረሻ መፍትሄ ሳያገኝ በእንጥልጥል ላይ ባለበት ወቅት፣ አሁን ደግሞ አካባቢው ለወርቅ አሰሳ እንደሚፈለግ በመነገሩ በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ነዋሪዎች የመፈናቀል አደጋ አጋጥሞአቸዋል።

አንድ ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ ወጣት ለኢሳት እንደገለጠው ሚድሮክ ኢትዮጵያ ከዚህ በፊት በህብረሰተቡ ላይ የፈጸመው በደል አንሶ አሁን ደግሞ ተመሳሳይ በደል ለመፈጸም እያደረገው ያለው እንቅስቃሴ አምና ያነሳነውን አይነት ተቃውሞ እንደገና ለማንሳት ይገፋፋናል ብሎአል።”

ሼክ ሙሀመድ አላሙዲ ደሀውን ህዝብ ያለመጠለያና ያለምንም ገቢ እያፈናቀሉ እርሳቸው ከወርቁ በሚያገኙት ገቢ በአለም ላይ ያላቸው ደረጃ መጨመሩ በዜና ይነገራል፣ በእኛ ህይወት ላይ በሚፈጽሙት ወንጀል ዙሪያ ግን ደረጃ አይወጣላቸውም፣ አካባቢያችን የጥቂቶች መበልጸጊያ የአብዛኛው ህዝብ መቀበሪያ እየሆነው ሲል አክሎአል።

በጉጂ ዞን ሻኪሶ ወረዳ በሚገኘው ሬጂ ቀበሌ በርካታ ቤተሰቦች ተፈናቅለው ለረሀብ ተጋልጠዋል። በሳቦሩ ወረዳ እንዲሁም በርካታ ሰዎች ከቦታቸው ተፈናቅለዋል። በቦረና ዞን መልካሳ ወረዳ ሁሎመዴዳ፣ ኡዴቻ፣ ሎቶሪ፣ ኦዶ፣ ሀንቃሬ፣ እና በሌሎች በርካታ ቀበሌዎች የሚኖሩ ሰዎች አካባቢያቸውን በአስቸኳይ እንዲለቁ በመጠየቃቸው ተደናግጠዋል።

የዞኑ የጸጥታ ሀይሎች ከሚድሮክ ጋር በመተባበር ህዝቡን እያንገለቱ ነው በማለት የአካባቢው ነዋሪዎች ተቃውሞአቸውን አሰምተዋል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide