የብኢኮ 90 በመቶ የአመራር ቦታዎች በአንድ አካባቢ ሰዎች የተያዙ መሆናቸውን ሰነዶች አመለከቱ

ጥር ፭ (አምስት)ቀን ፳፻ / ኢሳት ዜና :- በአብዛኛው በቀድሞ መንግስታት የተገነቡትን ስድስት  ወታደራዊ አገልግሎት ሰጪ የማምረቻ ኮምፕሌክሶችን ማለትም  ወታደራዊ ተሸከርካሪዎችን በማደስ ሲሰራ የነበረው- ቢሾፍቱ (40720)፣  ተተኳሾችን በማምረት ሲያገለግል የነበረው-  ሆርማት ፋብሪካ  ፣ ቀላል መሳሪዎችን በማምረት ተልእኮ የነበረው – ጋፋት ፋብሪካ ፣  ወታደራዊ አይሮፕላኖችን ለማደስ የተቋቋመው- ደጀን  ፋብሪካ፣  መለዋወጫዎችን ለማምረት የተመሰረተው – አዲስ ሜታል ፋብሪካ እንዲሁም ወታደራዊ አልባሳት ሲያመርት የነበረውን  አዳማ ጋርመንት ፋብሪካን በአንድ ላይ በመቀላቀል በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 183/2002 ብረታ ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን (ብኢኮ)፣ በእንግሊዝኛኛ ምህጻረ ቃል ሜቴክ በብር 10 ቢልዮን፣ የተፈቀደ (Autorized capital) እና በብር 3,178,914,604.55 ( ሶስት ቢሊዮን 178 ሚሊዮን 914 ሺ 604 ብር ከ 55 ሳንቲም) የተከፈለ ካፒታል (paid up capital) በ2002 ዓም የተቋቋመ ነው። ድርጅቱ እስከ 2008 ዓም መጨረሻ ድረስ 44 ቢሊዮን 993 ሚሊዮን 691 ሺ 179 ብር ከ41 ሳንቲም ሀብት እንዳለው ከድርጅቱ የ5 አመታት ሪፖርት ለመረዳት ይቻላል።

ኮርፖሬሽኑ  ኢንጂነሮች፣ ሞያተኞችና ድጋፍ ሰጪ አካላትን ጨምሮ 1,437 የሰራዊት አባላት እንዲሁም  2,474 ሲቪል ሰራተኞች በአጠቃላይ 3,911 ሰርተኞችን አሉት። ኢብኮ በአገሪቱ የሚካሄዱ የግንባታ ፕሮጀክቶችን ማለትም የአባይ ግድብ፣ የተርማል ሃይል ማመንጫ፣ የስኳር ፋብሪካዎችን ፣ የማዳበሪያ ፋብሪካ፣ የፍሌክሲብል ማኑፋክቸሪንግ አነስተኛ ፋብሪካዎች ግንባታ፣ የተሽከርከሪዎች ምርት፣ የእርሻ መሳሪያዎች ምርት እና ሌሎችንም ስራዎች በሃላፊነት ወስዶ ይሰራል።

በአገሪቱ ውስጥ አብዛኛውን ኢኮኖሚ የሚያንቀሳቅሰው ኢብኮ ( ሜቴክ) በመከላከያ ሚኒስቴር ስር የሚገኝ የመንግስት ተቋም ቢሆንም፣ የድርጅቱ መሪዎች የብሄር ስብጥር ሲታይ ኢትዮጵያን የሚወከል ደርጅት አይመስልም። በዋና ዋና የድርጅቱ ፋብሪካዎች በአመራርነትም ይሁን በምክትል ሃላፊነት የተቀመጡት መሪዎች 90 በመቶ የሚሆኑት የህወሃት አባላት፡የሆኑ የትግራይ ተወላጆች ናቸው።

ከኢብኮ ዋና ዳይሬክተር ሜጀር ጀኔራል ክንፈ ዳኘው ጀምሮ፣ ም/ል ዋና ዳይሬክተሩ – ብ/ጄ/ ጽጋቡ ፈትለ ፣ ፋይናንስ ክፍል ሃላፊው – ኮ/ል ሙዕዝ፣ ሎጂስቲክስ ክፍል ሃላፊው – ኮ/ል በረሃ፣ የሜጋ ፕሮጅክቶች ሃላፊ- ኮ/ል ሙሉ፣ የሰው ሃይል አስተዳደር ሃላፊ – ኮ/ል ተክላይ፣ ኦዲትና ኢንስፔክሽን ክፍል ሃላፊ – ኮ/ል በረሃ፣ ህግ ክፍል ሃላፊ – ኮ/ል ሙሃመድ፣ ስነምግባር ክ/ል ሃላፊ – ኮ/ል ህሉፍ፣ ኮንትራት አስተዳዳር ሃላፊ – ሌ/ኮ አክብረት፣ ፣ የእቅድ ዝግጅት ሃላፊ – ሌ/ኮ ተከስተ፣ የአቅም ግንባታ ማእከል ሃላፊ-  ሻ/ቃ ገብረስላሴ፣ ልዩ ጽ/ቤት ሃላፊ – ሻለቃ ክፍሌ፣ የቦርድ ጽ/ቤት ሃላፊ-  ሻለቃ መኮንን፣ እንዲሁም የሴቶች ጉዳይ ሃላፊ – ወ/ሮ ሲሳይነሽ በሙሉ የትግራይ ተወላጆች ሲሆኑ፣ ም/ል ዋና ዳይሬክተር ብ/ጄኔራል ጠና፣ ማርኬቴንግ ሃላፊ – ኮ/ል መኮንን፣ ምርምር ልማት ሃላፊ – ሻለቃ ታየ፣ የጥራት ም/ል ሃላፊ – ሻ/ቃ ምናሉ የኦሮሞ ተወላጆች ሲሆኑ ፣ የህዝብ ግንኑነት ሃላፊው አቶ ሚካኤል ደግሞ የአማራ ተወላጅ ናቸው።

በኢንዱስትሪ ዘርፍ ያሉ የአመራር ቦታዎችም 90 በመቶው የተያዙት በእነዚህ የትግራይ ተወላጅ የህወሃት አባላት ነው።   የቢሾፍቱ አውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ ሃላፊ – ኮ/ል ገብረመድህን፣ ደጀን አቪየሽን ኢንዱስትሪ- ኮ/ል ኪዱ፣ ህብረት ማንፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ – ሻለቃ ተሰማ፣ ጋፋት አርማመንት ኢንዱስትሪ-  ሌ/ኮ ግሩም፣ ሆሚቾ አሙኒሽን ኢንዱስትሪ – ኮ/ል ሃድጉ፣ ኮንስትራክሽን ማሽነሪ ኢንዱስትሪ – ሻ/ቃ ካህሳይ፣ ሎ/ኮሞቲቭ ኢንዱስትሪ – ሻለቃ ጸጋዬ፣ ፓወር ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ – ሻለቃ አሰፋ እስፔሻል ኢኩፕመንት ኢንዱስትሪ – ሻለቃ ይስሃቅ እንዲሁም  አቃቂ ቤዚክ ሜታል ኢንዱስትሪ ሻለቃ አሰፋ፣ በሙሉ የትግራይ ተወላጆች ሲሆኑ፣ ሃይቲክ ኢንዱስትሪ ሃላፊ- ኮ/ል ተመስገን የአማራ፣ ሜታል ፋብሪኬሽን ኢንዱስትሪ ሃላፊ ሻለቃ ቢቂላ እንዲሁም የአዳማ እርሻ መሳሪያዎች ኢንዱስትሪ ሃላፊ ሻ/ቃ አገሬ የኦሮሞ ተወላጆች ናቸው። የኢትዮ ፕላስቲክ ኢንዱስትሪ ሃላፊ ሻለቃ ተስፋየ ደግሞ ወላይታ ናቸው።

ሜቴክ ከፍተኛ ሙስና የሚፈጸምበትና በገልልተኛ ኦዲተር የማይመርመር  ተቋም መሆኑን  ምንጮች ይገልጻሉ።