የቡሌ ሆራ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ግቢያቸውን ለቀው ወጡ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 11/2010)የቡሌ ሆራ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ዛሬ ግቢውን ለቀው መውጣታቸው ታወቀ።

ለአንድ ሳምንት ትምህርት አቁመው ጥያቄያቸው እስኪመለስ ቢጠብቁም ምላሽ ባለማግኘታቸው ግቢውን ሙሉ በሙሉ ለቀው ለመውጣት ተገደዋል።

በጋምቤላ ዩኒቨርስቲ የታጠቁ የልዩ ሃይል አባላት ወደ ግቢው ዘልቀው በመግባት ተማሪዎችን እየደበደቡ መሆናቸውም ታውቋል።

በመቱ ዩኒቨርሲቲ ግቢውን ለቀው የወጡ ተማሪዎች አልተመለሱም። በግቢው የቀሩትም ትምህርት አለመጀመራቸው ታውቋል።

ከአንድ ሳምንት በላይ ትምህርት አቋርጠው የቆዩ የቡሌ ሆራ (ሀገረማርያም) ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ለማ መገርሳ መጥተው እንዲያናግሯቸው ጠይቀው ሲጠብቁ ነበር።

ፕሬዝዳንቱ አልመጡም። የሚወክላቸውን ሰውም አላኩም። የአስተዳደር ጥያቄን ጨምሮ የሶማሌ ክልል ልዩ ሃይል የሚያደርሰውን ጥቃት በመቃወም የቆዩት የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ለጥያቄያቸው መልስ የሚሰጣቸው አካል ማጣታቸውን ተከትሎ ዛሬ ህዳር 11/2010 ዩኒቨርስቲውን ለቀው መውጣታቸውን የኢሳት ምንጮች ከስፍራው ካደረሱን መረጃ ለማወቅ ተችሏል።

ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ከሌሊቱ 7 ሰዓት ላይ የመከላከያ ሰራዊት አባላት ወደ ዩኒቨርሲቲው ቅጥር ገብተው ተማሪዎችን መደብደባቸውን ተከትሎ በቡሌ ሆራ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎችም ትምህርት በማቆም ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ድጋፋቸውን መግለጻቸው የሚታወስ ነው።

ተማሪዎች ትምህርት እንዲጀምሩ ለማድረግ የተደረገው ሙከራ ባለመሳካቱ ዛሬ ዩኒቨርስቲውን ለቀው ወጥተዋል።

በሌላ በኩል በጋምቤላ ዩኒቨርስቲ የታጠቁ የልዩ ሃይል ፖሊስ አባላት ወደ ግቢው እየገቡ ተማሪዎችን እየደበደቡ መሆናቸው ተገለጸ።

በተማሪዎች መሃል የእርስ በርስ ግጭት ለመፍጠርም በልዩ ሃይል አባላት እንቅስቃሴ መጀመሩን የዩኒቨርሲቲው የኢሳት ምንጮች ከላኩት መረጃ ለማወቅ ተችሏል።

ከመቱ ዩኒቨርስቲ በመሸሽ ጋምቤላ የገቡ የትግራይ ተወላጆችን በመቃወም የተጀመረውን አነስተኛ ግጭት ተከትሎ ወደ ጋምቤላ ዩኒቨርስቲ የገቡት የልዩ ሃይል አባላት የአማራና የኦሮሞ ተማሪዎችን እየመረጡ በመደብደብ ላይ መሆናቸውም ታውቋል።

ትናንት ሌሊት በግቢው የተማሪዎች ጩኸት ይሰማ እንደነበረ የገለጹት ምንጮች የልዩ ሃይል አባላት በሌሊት ገብተው በርካታ ተማሪዎችን መደብደባቸውንም ጠቅሰዋል።

በመቱ የኒቨርስቲ ለሳምንታት የዘለቀው የትምህርት መቋረጥ አሁንም እንደቀጠለ ነው።

ብሄርን መነሻ አድርጎ የተጀመረው ግጭት የዩኒቨርሲቲውን የመማር ማስተማር ሂደት እንዲቋረጥ ያደረገው ሲሆን በተለይ የአማራ ተወላጆች የሆኑት ግቢውን ለቀው በመውጣታቸው ሁኔታዎች መባባሳቸውን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

ዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች እንዲመለሱ ቢጠይቅም ለደህንነታቸው ሰግተው የወጡ ተማሪዎች እንደማይመለሱ ገልጸዋል።

አብዛኞቹ ተማሪዎች በመቱ ከተማ ነዋሪ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑም ታውቋል።

ለሳምንታት ትምህርት አቋርጠው የቆዩት የሃሮማያ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች በአባገዳዎች ጥረት ባለፈው ሳምንት አጋማሽ ላይ ትምህርት መጀመራቸው ታውቋል።

አባ ገዳዎቹ ተማሪዎች ያነሱዋቸው ጥያቄዎች አንድ በአንድ እንደሚፈቱላቸው ቃል በመግባት ለሳምንታት ሲካሄድ የነበረው የትምህርት ማቆም አድማ እንዲቋረጥ አድርገዋል።

ተማሪዎቹ መከላከያ ሰራዊት ከግቢያቸው እንዲወጣ፣ በግቢያቸው ውስጥ የተደራጀውና“ፒስ ፎረም” ወይም የሰላም ፎረም የሚባለው የህወሃት የስለላ መዋቅር እንዲፈርስ ጥያቄ አቅርበው ነበር።

መከላከያ ሰራዊት ከግቢው እንደሚወጣ እንዲሁም ፒስ ፎረም የሚባለውም የስለላ መዋቅር እንደሚፈርስ ቃል ተገብቶላቸዋል ትምህርት ጀምረዋል ሲሉ የኢሳት የመረጃ ምንጮች ገልጸዋል።