የሕዋሃት ታጋዮች አጥንታቸውን የከሰከሱት ትግራይን ለማልማት ነው ተባለ

(ኢሳት ዜና–ነሐሴ 11/2009) የሕዋሃት ታጋዮች አጥንታቸውን የከሰከሱት ትግራይ እንድትለማ ነው በማለት በአንድ ወቅት ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ መናገራቸውን የአዲስ አበባ ኢህአዴግ ጽሕፈት ቤት በድረገጹ አስታወቀ።

 

ጽህፈት ቤቱ በፌስቡክ ድረገጹ እንደገለጸው በ1984 በትግራይ መቀሌ የሕወሃት ምስረታ በአል ሲከበር አቶ መለስ ለትግራይ ወጣቶች የተከሰከሰው አጥንት ለትግራይ ልማት ሲባል መሆኑን በይፋ ተናግረዋል።

 

በዚያን ወቅት አቶ መለስ እኔ የተፈጠርኩት ከዚህ ወርቅ ህዝብ በመሆኑ እድለኛ ነኝ በማለት ከሌላው ኢትዮጵያዊ የተለየን ነን በሚል ንግግር ማድረጋቸው ይታወሳል።

 

የአቶ መለስ ዜናዊን 5ኛ አመት የሙት አመት ዝክረ መለስ በሚል በተለያዩ ዝግጅቶች እያከበረ ያለው የሕወሃት/ኢህአዴግ መንግስት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ያደረጓቸውን ንግግሮች እንዲታወሱ በማድረግ ላይ ይገኛል።

 

በዚህ ሁኔታም የአዲስ አበባ ኢሕአዴግ ጽህፈት ቤት በድረገጹ አቶ መለስ የሕወሃት ታጋዮች አጥንታቸውን የከሰከሱት ትግራይን እንድትለማ ለማድረግ ነው ማለታቸውን አስታውሷል።

 

አቶ መልስ በወቅቱ ያደረጉት ንግግር የሕወሃት ትግል ከትግራይ ልማት ውጪ ሌላ አጀንዳ እንዳልነበረው የሚያሳይ መሆኑን እንዳመላከተ ታዛቢዎች በመግለጽ ላይ ናቸው።