የህወሃት ወታደራዊ አመራሮች ለወርቅ ልማት በቤኒሻንጉል መስፈራቸው ተገለጸ

ኢሳት (መስከረም 9 ፥ 2009)

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጊዛን ተብሎ በሚጠራ አካባቢ ወደ አንድ ሺ የሚጠጉ የህወሃት ወታደራዊ አመራሮችና አባላት በአካባቢው ለወርቅ ልማት በሚል መስፍራቸው በነዋሪዎች ዘንድ ተቃውሞ መቀስቀሱ ተገለጸ።

ጉዳዩን በመከታተል ላይ የሚገኘው የቤኒሻንጉል ህዝቦች የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋም በጊዛን የተቀሰቀሰውን ተቃውሞ ተከትሎ ወደ 300 አካባቢ የሚጠጉ ሰዎች ወደ አሶሳ እስር ቤት መወሰዳቸውን ለኢሳት አስታውቋል።

የድርጅቱ ሃላፊ የሆኑት አቶ ካሊድ ነስር የጊዛን አካባቢ ያለውን የወርቅ ሃብት ለመጠቀም በማሰብ የህወሃት አመራሮች አካባቢውን ኢላማ ማድረጋቸውን ከዜና ክፍላችን ጋር ባደረግነው ቃለምልልስ አስረድቷል።

ይሁንና ነዋሪዎች ድርጊቱን በመቃወም ቁጣ ማሰማት ቢጀምሩም የሃይል እርምጃ በመውሰድ ላይ መሆኑን የተናገሩት ሃላፊው ለእስር ከተዳረጉት መካከል ከ10-20 የሚሆኑት መሞታቸውን ገልጸዋል።

ለእስር የተዳረጉ ሰዎች ስም ዝርዝር ይፋ ያደረጉት የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቱ፣ ነዋሪዎቹ የሽብት ድርጊት እንደፈጸሙ ተደርገው መጉላላት እየደረሰባቸው እንደሚገኝ አስታውቀዋል።

የአካባቢው ነዋሪዎች ክልሉ ካለው የወርቅ ልማት ተጠቃሚ አይደሉም ሲሉ የገለጹት  አቶ ካሊድ፣ በጋምቤላና ሌሎች አካባቢዎች ተግባራዊ ሲደረጉ የነበሩ የመሬት ቅርምቶች በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በሰፊው መከናወኑንና የህወሃት አመራሮች ሃብቱን እየተተጠቀሙ መሆናቸውን አክለው ተናግረዋል።

የክልሉ መንግስት የህወሃት ባለስልጣናት የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ ማስቆም እንደማይችሉና አንድ ኮሎኔል ይህንኑ ድርጊት ለመቆጣጠር በስፍራው እንደተሰማራ መደረጉን አቶ ካሊድ በቃለምልልሳቸው አስረድተዋል። ከሁለት አመት በፊት በክልሉ የወርቅ ቁፋሮን ለማካሄድ ከመንግስት ጋር ስምምነትን የፈጸመ አንድ የግብፅ ኩባንያ በሃገሪቱ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ የወርቅ ክምችት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ማግኘቱን ይፋ እንዳደረገ ይታወሳል።

አስኮም የተሰኘ ይኸው ኩባንያ ከመንግስት ጋር የወርቅ ሃብቱን ጥቅም ላይ ለማዋል በወቅቱ ከነበረው የማዕድን ሚኒስቴር ጋር ውል መፈጸሙም መዘገቡ ይታወሳል።

በቅርቡ በክልሉ የተቀሰቀሰውን ተቃውሞ እና እስራት በተመለከተ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልም ሆነ የፌዴራል መንግስት የሰጡት ምላሽ የለም።