ዓርበኞች ግንቦት 7 በለንደን በተሳካ ሁኔታ ሕዝባዊ ስብሰባውን አካሄደ

ኅዳር ፳ (ሃያ)ቀን ፳፻ / ኢሳት ዜና :- ዓርበኞች ግንቦት 7 በእንግሊዝ ዋና ከተማ ለንደን ውስጥ ሕዝባዊ ስብሰባውን  እ.ኤ.አ. ኖቨንበር 27 ቀን 2016 በድምቀት አካሄደ። በስፍራው ላይ የአፍሪካ ኢንስቲቱት ሴኩሪቲ ስተዲስ ዳሬክተር የሆኑት የተከበሩ ሻለቃ ዳዊት ወ/ጊዮርጊስ፣ ሚስ ካትሪን ፕሉየር በለንደን ዩናይትድ ኔሽን አሶሴሽን የሳውዝ ኢስት ሪጅን ዳሬክተር እና የዓርበኞች ግንቦት 7 ከፍተና አመራር አባል አቶ ብዙነህ ጽጌ በስብሰባው ላይ በክብር እንግድነት ተገኝተዋል።

በእለቱ በተጋባዥነት በስፍራው የተገኙት እንግዶች ለተሰብሳቢዎቹ ስለ ወቅታዊው የኢትዮጵያ ሁኔታ አስመልስክቶ ንግግር አድርገዋል።የተከበሩ ሻለቃ ዳዊት ወጊዮርጊስ በቅርቡ ስለተቋመው አገራዊ ኅብረት እና ስለ መጪዋ የኢትዮጵያ መፃኢ እጣፈንታ እና መወሰድ ስላለባቸው እርምጃዎች አስመልክቶ ሰፋ ያለ ማብራሪያ ሰጥተዋል።

ቀጣይ ተናጋሪ የነበሩት የዓርበኞች ግንቦት 7 ከፍተኛ አመራር አባል አቶ ብዙነህ ጽጌ በበኩላቸው የድርጅታቸውን አጠቃላይ ሁኔታን ጨምሮ አሁን ያለበትን ደረጃ እና እየተከፈለ ስላለው የትግል መስዋእትነት በዝርዝር አቅርበዋል። ስለ ኢትዮጵያ የወደፊት ህልውና ጋር በተያያዘ ሊወሰዱ ስለሚገቡ ተጨባጭ አጣዳፊ እርምጃዎች አስመልክቶ ድርጅታቸው ስለሚወስዳቸው የትግል ስልቶች አጽኖት ሰጥተው ተናግረዋል።

ሚስ ካትሪን ፕሉየር በበኩላቸው በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ያለው የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ከነበረው በከፋ ሁኔታ እየተባባሱ መምጣታቸውን አብራርተው ድርጅታቸው ከኢትዮጵያዊያን የጋራ ንቅናቄዎች ጋር በጥምረት ለመስራት ፈቃደኛ እንደሆነም አክለው ገልጸዋል።

በአዳራሹ ቁጥራቸው ከሶስት መቶ በላይ ተሰብሳቢዎች መገኘታቸውንና ያላቸውን አስተያየቶችና ጥያቄዎች ለተሰብሳቢዎቹ አቅርበው ምላሽ እንደተሰጣቸውም ሪፖርተራችን ከስፍራው ዘግቧል።