ከ2 አመት በፊት ከቴሌ የተባረሩ በሺሆች የሚቆጠሩ ሰራተኞች በቴሌ በሚወጡ ስራዎችን ላይ ተወዳድረው እንዳይቀጠሩ እንደተከለከሉ ተናገሩ

ጥቅምት ፪ (ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የኢትዮፕያ ቴሌኮሚኒኬሽን መስሪያ ቤት የ1.6 ቢሊዮን ዶላር የቴሌኮሚኒኬሽን ውል፤ ዜድ ቲ ኢ እና ሁዌይ ለተሰኙ ሁለት የቻይና ኩባንያዎች እንደሰጠ የታወቀ ሲሆን፤ ከ2 አመት በፊት ከቴሌ የተባረሩ በሺሆች የሚቆጠሩ ሰራተኞች ደግሞ በችግር ከመሰቃየታቸውም በላይ፤ በቴሌ የሚወጡ ስራዎችን ተወዳድረው እንዳይቀጠሩ እንደተከለከሉ ተናገሩ።

የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚ/ሩ ደብረጽዮን ገብረሚካኤል በአሜሪካን ኮንግረስ በስለላና የአሜሪካንን ቴክኖሎጂ ሰርቆ ለቻይና በመስጠት ለተከሰሰው ዚቲኢና ለሁዌይ ኩባንያ፤ ይሄንን የ1.3 ቢሊዮን ዶላር ውል የሰጡት በኢትዮጵያ የሚገኙትን የእጅ ስልክ ተጠቃሚዎች ቁጥር በእጥፍ ለማሳደግ በሚልና ለሌሎች ተያያዥ ምክንያቶች እንደሆነ ታውቋል።

በሌላ ዜና፤ ከ23 ወራት በፊት ያለበቂ አገልግሎት ክፍያና ያለጡረታ ከቴሌኮሚኒኬሽን መስሪያ ቤት የተባረሩ በሺሆች የሚቆጠሩ ሰራተኞች ከቤተሰቦቻቸውና ልጆቻቸው ጋር በችግር እየተጠበሱ መሆናቸውን አንድ የቀድሞ የቴሌ ሰራተኛ ገለጹ።

ማንነታቸው እንዳይገለጥ የፈለጉ ከቴሌ የተባረሩ ሰራተኛ ለኢሳት እንደተናገሩት፤ ከሁለት አመት በፊት የቴሌ አስተዳደር (ማኔጅመንት) ለፈረንሳይ ኩባንያ ከተሰጠ በሁዋላ፤ 12 ሺህ ሰራተኞች ከስራቸው በተነሱ ግዜ፤ ወደፊት የስራ እድሎች ሲፈጠሩ እንደሁኔታው እየታየ ወደስራ ገበታችሁ ትመለሳላችሁ የሚል ቃል ቢገባላቸውም፤ ሚ/ሩ አቶ ደብረጽዮን ገብረሚካኤል ቃላቸውን አጥፈው እንደገና ተወዳድረን እንኩዋን እንዳንቀጠር ከልክለውናል ብለዋል።

ግለሰቡ ቴሌኮሚኒኬሽን አዲስ ባወጣው የ3000 ሰዎች የስራ ማስታወቂያ ላይ፤ ከፍተኛውን የእድሜ ገደብ 27 አመት፤ የስራ ልምዱን ደግሞ ዜሮ አድርጎ፤ የ2003 እና 2004 ተመራቂዎችን ብቻ እንሚቀጥር አስታውቋል።

ከትጥቅ ትግሉ ጀምሮ የሕወሀት ደህንነትና ስለላ ስራዎች ሀላፊ የሆኑትና አሁንም የስልኩና የኢንተርኔት ግንኙነቶችን የመጥለፍ ስራዎችን፤ እንዲሁም የአሜሪካን ድምጽን፤ ኢሳትንና ሌሎች መገናኛ ብዙሀንን የመሸበብ ስራ ይቆጣጠራሉ በሚባሉት አቶ ደብረጽዮን ገብረሚካኤል የሚመራው ቴሌ ባወጣው የስራ ማስታወቂያ ላይ ያስቀመጣቸው ገደቦች፤ የቀድሞ ሰራተኞች እንዳያመለክቱ ሆን ተብሎ የተደረጉ ናቸው ሲሉ ሰራተኞቹ ከሰዋል።

የመከላከያ ሰራዊት ጄኔራሎችና የደህንነት መስሪያ ቤት ሃለፊዎች፤ በተለይም ለኢህአዴግ ታማኝነት ያላቸውን ወጣቶች በመመልመል፤ በቴሌኮሚኒኬሽን መስሪያቤት በመሰግሰግ፤ የጠለፋና መሰል የስለላ ስራዎች ላይ እንዳሰማሩና ወደፊትም ይሄው አሰራር እንደሚቀጠልበት ለትምህርት ተልከው በስደት የሚቀሩ የቀድሞ የቴሌ ሰራተኞች ለኢሳት ገልጸዋል።