ከ12 ቢሊዮን ብር በላይ ያልተወራረደና የተበላሸ ሂሳብ ያለው ንግድ ባንክ ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ ተጨማሪ ወጪ ማውጣቱ ታወቀ

ግንቦት ፫(ሦስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ለኢሳት የደረሰው የባንኩ የውስጥ ኦዲት ሪፖርት እንደሚያሳየው በበጀት አመት እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2013 እና 2014 ባንኩ ያላወራረደው 11 በሊዮን ብር እንዲሁም የተበላሸ ገንዘቡ 1 ቢሊዮን ብር ቢደርስም፣ የባንኩ ባለስልጣናት ከተመደበላቸው መደበኛ በጀት ውጭ 729 ሚሊዮን ብር አውጥተዋል። “ሙስናን በመዋጋት አገራችንን ከዘላለማዊ ከእዳ እንታደግ “ በሚል የባንኩ ሰራተኞች የውስጥ እንቅስቃሴ የጀመሩ ሲሆን፣ ከመንግስት ባለስልጣናትና ከህወሃት ታዋቂ ባለሀብቶች ጋር ከፍተኛ የጥቅም ቁርኝት የፈጠሩት የንግድ ባንኩ ስራ አስኪያጅ፣ ባንኩንና አገሪቱን ለከፍተኛ እዳ እየዳረጉዋት ነው ይላሉ።
የባንኩ የውስጥ ሪፖርት እንደሚያሳየው በበጀት አመቱ ባንኩ ለተለያዩ ወጪዎች በሚል 1 ቢሊዮን 200 ሚሊዮን ብር መድቦ የነበረ ቢሆንም፣ በበጀት አመቱ መጨረሻ ግን 1 ቢሊዮን 900 ሚሊዮን ወይም ከተፈቀደለት በጀት 67 በመቶ በላይ ወጪ ማድረጉ በኦዲት ሪፖርቱ ላይ ተመለክቷል። ባንኩ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ የሆነውን ገንዘብ ያጠፋው ያልተሰበሰቡ ብድሮችን ለማስመለስ ነው ቢልም፣ ይህን የሚያረጋገጥ ማስረጃ እንደሌለ ሰራተኞች ይገልጻሉ። የባንኩ ከፍተኛ ሹሞች በተለያዩ ፕሮጀክቶች ስም ከባለስልጣናትና ታዋቂ ሰዎች ጋር በመመሳጠር እየዘረፉ መሆኑን የሚናገሩት ሰራተኞች፣ እስካሁን ድረስ አንድም ከፍተኛ አመራር ተጠያቂ አለመሆኑን ይገልጻሉ።
ባንኩ በየጊዜው ከፍተኛ የሆነ ገንዘብ አተረፍኩ በማለት መግለጫ እንደሚሰጥ የሚናገሩት ሰራተኞች፣ ባንኩ ባተበላሸ እና ባልተወራረደ ብድር ስም የከሰረውን ገንዘብ ግምት ውስጥ ሳያስገባ ለህዝብ ግንኙነት ስራ ብሎ የሚሰጠው መግለጫ መሆኑን ይናገራሉ።
የተለያዩ ባንኮች በንግድ ባንክ ያስቀመጡት 926 ሚሊዮን ብር መኖሩን የሂሳብ ሪፖርቱ ቢያሳይም፣ ይህ ገንዘብ በባንኩ ውስጥ እንደሌለ ሰራተኞች ይናገራሉ። ብሄራዊ ባንክ አስቸኳይ ፍተሻ እንዲያደርግም ያሳስባሉ።