ከአዲስ አበባ ወደ ጅጅጋ የሚወስደው መንገድ በባቢሌና በሃረር መካከል መዘጋቱን የአሜሪካ ኤምባሲ አስታወቀ

(ኢሳት ዜና–ነሐሴ 4/2009)ከአዲስ አበባ ወደ ጅጅጋ የሚወስደው መንገድ በባቢሌና በሃረር መካከል መዘጋቱን የአሜሪካ ኤምባሲ አስታወቀ።
በጦር መሳሪያየተደገፈ ከፍተኛ የተኩስ ለውውጥ እየተካሄ መሆኑንና መከላከያ ሰራዊት ወደ አካባቢው መንቀሳቀሱን ኤምባሲው ገልጿል። የአሜሪካ ዜጎች በባቢሌና ሃረር መካከል ባሉ ቦታዎች እንዳይጓዙ ኤምባሲው አስጠንቅቋል።
በባህርዳርም አፈሳው ተጠናክሮ ቀጥሏል። የሆቴል ባለቤቶችና ከፍተኛ ነጋዴዎችም እየታሰሩ ነው።
በሀዋሳ የባጃጅ ተሽከርካሪዎች የስራ ማቆም አድማ አድርገው ውለዋል። የመንግስት ተሽከርካሪዎችና የከተማ አውቶቡስ ላይ ጥቃት ተሰንዝሯል።በተለያዩ ከተሞች የተጀመረው የስራ ማቆም አድማም እንደቀጠለ ነው።
በባህርዳር ውጥረቱ ጨምሯል።
የአድማ በታኝ ዩኒፎርም የለበሱ የአጋዚ ወታደሮች ውርውር ይላሉ ፍተሻውም ፣ እስራቱም ቀጥሏል።
ነሃሴ 1 የሰማዕታት ቀን የስራ ማቆም አድማ ያደረጉ በጥቃቅንና አነስተኛ የተደራጁ የህወሓት/ብአዴን አባላት ሱቆቻቸው ታሽጎባቸዋል።
በቀበሌ 12 ከመናሃሪያው አካባቢ ጋሳ ሆቴል ጥግ የሚገኙት የፀጉር ቤት ኮንቲነሮች ፤ ትንንሽ ምግብ ቤቶች… ሰማዕታት የምትሏቸውን አስባችኋል፣ አድማ ተሳትፋችኋል በማለት ኮንቲነሮቻቸው የታሸገባቸው ሲሆን ወረቀቱን የሚቀድ ይቀጣል በማለት የግሽ አባይ ክ/ከተማ ካድሬዎች እና ፖሊሶች እያስፈራሩ ሲሆን ” ወረቀቱን አንሱል እና እንስራበት ” በማለት ሲጠይቁ ” ግንቦት 7 መጥቶ ያስከፍትላችሁ ” የሚል ምላሽ ነው በካድሬዎቹ የተነገራቸው። በቀበሌ 11 አባይ ማዶ በገበያው ዙሪያ አድማ አድርጋችኋል የተባሉ ” የህዝብ አገልግሎት ባለመስጠት ታሽጓል ” የሚል ወረቀት የተለጠፈባቸው ሲሆን ወደ ህዳር 11 ክ/ከተማ ሂደው ካድሬዎቹን ሲጠይቁ በፅ/ቤቱ በሰፈረው የልዩ ሃይል አድማ በታኝ ዩኒፎርም በለበሱ የአጋዚ ወታደሮች ታፍነው ታስረዋል። በጠዋት ለመጠየቅ ከሄዱት ውስጥ አንዱ ሊይዙት ሲሉ በማምለጡ መረጃው ለሁሉም ተዛምቷል። የተያዙ ከ5 የሚበልጡ ባለኮንቲነሮች ድብደባም እንደተፈፀመባቸው ለማወቅ ተችሏል። ከባህርዳር በሚያስወጡና በሚያስገቡ መንገዶች ላይ በሚገኙ ከተሞች ፍተሻው ከፍተኛ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል። ወደ ሀዋሳ ለኢትዮጵያ ታዳጊዎች ሻምፒዮን ለመሳተፍ እያመራ የነበረው የአማራ ክልል ታዳጊዎች ቡድን በመንገድ ላይ ባለው አለመረጋጋት የተነሳ በደጀን ለማደር መገደዱም ተሰምቷል።
በደብረታቦር አድማው ለአራተኛ ቀን ቀጥሏል። ሱቆችና መደብሮች እንደተዘጉ ናቸው። በምስራቅ ጎጃም በበርካታ አካባቢዎች ግብር አንከፍልም በሚል የተነሳው ተቃውሞና የስራ ማቆም አድማ ተጠናክሮ እየተካሄደ ነው። በሸዋ ሮቢት ሳምንቱን ያለፈው አለመረጋጋት አሁንም አልበረደም። በርካታ ሱቆች እንደታሸጉ ናቸው።
በሀዋሳ ዛሬ የባጃጅ አሽከርካሪዎች የስራ ማቆም አድማ አድርገው መዋላቸው ታውቋል። ከአካባቢው የደረሰን መረጃ እንደሚያመልክተው የባጃጅ ትራንስፖርት ከአስፓልት መንገዶች ውጭ እንዲሆኑ መወሰኑን በመቃወም የተካሄደው የስራ ማቆም አድማ ግጭት ያስከተለ ሲሆን ፖሊስ ሌባ በሚል ተጀምሮ የመንግስት ተሽከርካሪዎች ላይ ጥቃት በመፈጸም መቀጠሉ ታውቋል። የከተማ አውቶብሶች መስታወታቸው መሰባብሩን የገለጹት ምንጮች የፌደራል ሃይል ተጨምሮ ማምሻውን ግጭቱ ቢበርድም ባጃጅ አሽከርካሪዎች ግን ስራ እንዳልጀመሩ ጠቅሰዋል።
የአሜሪካን ኤምባሲ ደግሞ ለዜጎቹ ማስጠንቀቂያ ማስተላልፉ ተሰምቷል። ኤምባሲው በድረገጹ ከበተነው የማስጠንቀቂያና የጥንቃቄ መልዕክት መረዳት እንደተቻለው፡ ከአዲስ አበባ ወደ ጅጅጋ የሚወስደው መንገድ ለደህንነንት አደጋ ስላለው የአሜሪካ ዜጎች በዚያ መስመር ጉዞ ካላቸው እንዳይንቀሳቀሱ አሳስቧል። ኤምባሲው እንዳለው አዲስ አበባ ጂጂጋ መስመር ባቢሌና ሀረር መሃል መንገድ ተዘግቷል። የተኩስ ልውውጥ እየተካሄደ ነው። ኤምባሲው ማስጠንቀቂያውን ከመስጠት ባለፈ እየተካሄደ ነው ስለተባለው የተኩስ ልውውጥ ዝርዝር መረጃ አላቀረበም። በሌላ በኩል የአሜሪካን ኤምባሲ ለጤና አገልግልት እንዲውል በሚል በእርዳታ የሰጠውን ተሽከርካሪ ለፖሊስና ወታደራዊ ጠቀሜታ እንዲውል መደረጉን ተከትሎም ማብራራያ እንዲሰጠው ጠይቋል። ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጥያቄውን ያቀረበው ኤምባሲው በአሜሪካ ድጋፍ የተሰጠው ተሽከርካሪ ከታሰበለት ዓላማ ውጪ መዋሉን በተመለከተ ምርመራ እንዲደርግ አሳስቧል። በአምቦ በተመሳሳይ ወታደሮችን ሲያጓጉዝ በነበረ የጤና ቢሮ ተሽከርካሪ ላይ ጥቃት ተሰንዝሮ መቃጠሉ የሚታወስ ነው።