አንድ ኢትዮጵያዊ በካናዳ ዊኒ ፔግ የ5 አመት አስራት ተፈረደበት

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 14/2010)የንግድ አጋሩን ለማስገደል ተንቀሳቅሷል በሚል የተወነጀለው ኢትዮጵያዊ በካናዳ ዊኒ ፔግ የ5 አመት አስራት ተፈረደበት።

በፖለቲካ ጥገኝነት በካናዳ የሚኖረው አቶ አማረ ገብሩ እስራቱን ሲጨርስ ከሀገር እንደሚባረርም ይፋ ሆኗል።

ይህን ቤተሰቡን ያስደነገጠውን የማባረር ርምጃ ለማስቀረትም ጠበቆች እስራቱን በይግባኝ ለማስቀነስ በመሯሯጥ ላይ መሆናቸውን የካናዳው ሲ ቲ ቪ ኒውስና ዊኒ ፔግ ፍሪ ፕሬስ በዘገባቸው አመልክተዋል።

አቶ አማረ ገብሩ ስሟ ካልተጠቀሰው የ31 አመት ኢትዮጵያዊ ስደተኛ ጋር በጋራ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2011 የገዙት የሸቀጣሸቀጥ ሱቅ በወራት ግዜ ውስጥ የውዝግብ መነሻ እንደሆናቸው ተመልክቷል።

አማረ ገብሩ ውዝግቡን ተከትሎ ከአንድ የላውንደሪ ቤቱ ደንበኛ ጋር በመተባበር የንግድ አጋሩን ለማዘረፍ መንቀሳቀሱ በኋላም ይህንን ሀሳቡን በመለወጥ ለማስገደልና ለገዳዩም 10 ሺ ዶላር ለመክፈል ማሴሩን የፍርድ ሂደቱን የተከታተሉት የዊኒ ፔግ ካናዳ ጋዜጦች ጽፈዋል።

ለግድያውም የተመለመለው የ28 አመቱ ወጣት ከ10ሺ ዶላር በተጨማሪ የቤት ግዢ እዳውን እንደሚሸፍንለት ቃል እንደገባለትም ገልጿል።

ለገዳይነት የታጨው የ28 አመቱ ወጣት ለግድያ ለምትፈለገው ግለሰብ ጉዳዩን በማስረዳቱና በጋራም ሁኔታውን ለፖሊስ በማሳወቃቸው ፖሊስ ባደረገው ክትትል ተጠርጣሪው በቁጥጥር ስር መዋሉ ታውቋል።

ፖሊሶች ጉዳዩን ካወቁ በኋላ ለገዳይነት የታጨው ግለሰብ ከፖሊስ በተሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ከተጠርጣሪው ጋር ግንኙነቱን በመቀጠል ሴራውን እየቀረጸ ለፖሊስ በመስጠቱ ርምጃው መከተሉም ተመልክቷል።

አቶ አማረ ገብሩ ድርጊቱን ሆን ተብሎ የተቀነባበረ ነው በማለት ቢያስተባብልም ፍርድ ቤቱ መከራከሪያውን ባለመቀበል የ5 አመታት እስራት መወሰኑ ታውቋል።

ከአምስት ወራት በፊት በሰኔ 2017 የንግድ አጋሩን ለመግደል አሲሯል በሚል የተከሰሰው አቶ አማረ ገብሩ በዊኒፔግ ካናዳ የልብስ እጥበት አገልግሎት የሚሰጥ ላውንደሪ ቤት ባለንብረት እንደሆነም ተዘግቧል።

ባለፈው ሰኞ የአምስት አመታት እስር የተበየነበት አቶ አማረ ገብሩ በካናዳ ጥገኝነት ያገኘው በፖለቲካ ስደተኝነት ቢሆንም በካናዳ ህግ 6 ወርና ከዚያ በላይ በወንጀል የተፈረደበት ከካናዳ እንደሚባረር ሕጉ ያስገድዳል።

የአቶ አማረ ገብሩ ጠበቃ ሚስተር ማይክ ኩክ የፍርድ ቤቱ ውሳኔ የደንበኛቸውን መባረር እንዳያስከትል ዳኝው ውሳኔያቸውን ከ6 ወራት በታች እንዲያደርጉ የተማጸኑ ቢሆንም ተቀባይነት አላገኙም።

ሆኖም ጠበቃው ውሳኔውን ለማስቀነስ ከተቻለም የጥፋተኝነቱን ውሳኔ ለማሻር ይግባኝ እንደሚሉ አስታውቀዋል።