አንድነት ግንቦት 12 ቀን የሚያዘጋጀው መድረክ በአራት እውቅ አርቲስቶች እንደሚመራ አስታወቀ

ግንቦት ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ፓርቲው፦”ኪነ-ጥበብ በማህበረሰቡ ውስጥ ያላት ሚና” በሚል መሪ ሀሳብ በሚቀጥለው እሁድ በብሄራዊ ቴአትር በሚያካሂደው ዝግጅት የአገሪቱ እውቅ አርቲስቶች ተገኝተው ከተሳታፊው ጋር ውይይት እንደሚያደርጉ ገልጿል።

ይሁንና መድረኩን የሚመሩት ዕውቅ አርቲስቶች እነማን እንደሆኑ ፓርቲው ለጊዜው ስማቸውን ከመግለጽ ተቆጥቧል።

በፓናል ውይይቱ ስለሚሳተፉት አራት ፓናሊስቶች ማንነት ፓርቲው ለጊዜው ከመግለጽ ቢቂጠብም፤ ከመካከላቸው ሰዓሊ፣ ደራሲና ጸሐፊ ተውኔት እንደሚገኙበት የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ ጠቁመዋል።

አርቲስቶቹ በርዕሰ-ጉዳዩ ላይ መንደርደሪያ ሀሰብ በመስጠት ውይይቱን ከመምራት በተጨማሪ ከተሳታፊዎች ለሚቀርቡላቸወ ጥያቄዎች ምላሽ እንደሚሰጡ  ሀላፊው ዶክተር ሀይሉ አርአያ ገልጸዋል።

በተለይ፦”ኪነ-ጥበብ በማህበረሰባችን ውስጥ ያለው ሚና ምንድነው? ሚናውን በትክክል እየተወጣ ነወይ?፣የሚጠበቅበትን ሚና ከመወጣት ያገደው ችግር ምንድነው? እና እነዚህን ችግሮች ለመፍታት ምን ኣይነት እርምጃ መወሰድ አለባቸው?”የሚሉት የውይይቱ አንኳር ነጥቦች መሆናቸውን ዶክተር ሀይሉ አመልክተዋል።

ህብረተሰቡ ለኪነ ጥበብ ያለው አመለካከት እና በእለት-ተእለት ህይወቱ ውስጥ የሚሰጠው ድርሻ አጠያያቂ በመሆኑ፤ ይህን መድረክ ማዘጋጀት አስፈላጊ ሆኖ እንደተገኘ የህዝብ ህንኙነት ሀላፊው አስረድተዋል።

“ኪነ-ጥበብ  የዕድገት መሳሪያ ነው።በሥነ-ጽሁፍ ያልዳበረ ህብረተሰብ በቁሳዊ እድገት ብቻ ወደፊት ሊራመድ አይችልም”ብለዋል-ዶክተር ሀይሉ።

ሼክስፒርና ማርክ ትዌይን የሠሯቸው የሥነ ጥበብ ውጤቶች በምዕራቡ ዓለም ዘለዓለማዊ ሆነው መቀጠላቸውንና ከዚያን ጊዜ ጀምሮም የደራሲዎቹን ሥራ መሠረት በማድረግ ኅብረተሰቡ ራሱን እየቀረፀና እያስተካከለ መምጣቱን ያወሱት ዶ/ር ኃይሉ፣ በአፍሪካም እነ ቼኔዋ አቼቤ፣ ኢትዮጵያ  ደግሞ እነ ሐዲስ ዓለማየሁ፣ ከደበ ሚካኤል፣ አቤ ጉበኛና የመሳሰሉ ደራሲዎች የኅብረተሰቡን አስተሳሰብ በማሳደግ ረገድ ከፍተኛ ሚና ተጫውተው ማለፋቸውን በምሳሌነት ጠቅሰዋል፡፡

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide