አቶ መለስ ዜናዊን ለመተካት አዲስ ህግ ተረቀቀ

ነሀሴ ፲ (አስር) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣን ለኢሳት እንደገለጡት ፍትህ ሚኒስቴር እጅግ ጥብቅ በሆነ ሚስጢር አዲስ ህግ አርቅቆ ለፓርላው የህግ ክፍል ልኳል።

በከፍተኛ ሚስጢር በተያዘው በዚህ ህግ የማርቀቅ ስራ ላይ የተሻለ የህግ እውቀት አላቸው የተባሉ ሰዎች  ተሳትፈዋል።

አቶ መለስን የመተካቱ ነገር ያለቀለት ጉዳይ መሆኑን ባለስልጣኑ ገልጠዋል። ፓርላመው ምናልባትም የፊታችን ማክሰኞ ካልሆነም በሚቀጥለው ሳምንት ውስጥ በአንደኛው ቀን ከእረፍት ለአስቸኳይ ስብሰባ ተጠርቶ ረቂቅ ህጉን ያጸድቀዋል።

ኢህአዴግን የመሰረቱት ሁሉም ፓርቲዎች በጉዳዩ ዙሪያ እየመከሩ መሆኑም ታውቋል። እስካሁን ድረስ ማን በእጩነት እንደቀረበ ለማወቅ አልተቻለም።

ከአቶ መለስ መጥፋት ጋር በተያያዘ የትራንስፎርሜሸኑ ዋና ዋና ሥራዎች መንቀሳቀስ እንዳልቻሉም ታውቋል።

በአምስት ዓመቱ የመንግስት የዕድገትና የትራንስፎርሜሸን ዕቅድ ውስጥ ቁልፍ እንደሆኑ የሚነገርላቸው አራት ተቋማት ያለሥራ መቀመጣቸውን
ባለስልጣኑ ገልጠዋል።

በአቶ አባይ ጸሐዬ የሚመራው የስኳር ኮርፖሬሸንን ጨምሮ የባቡር ኮርፖሬሽን፣የብረታብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሸን
እንዲሁም በቅርብ የተመሰረተው የግብርና ትራንስፎርሜሸን ኤጀንሲ የየራሳቸው ዳይሬክተሮች ቢሾሙላቸውም በቀጥታ
በአቶ መለስ የቅርብ ክትትል የሚደረግላቸው ተቋማት በመሆናቸው ከጠ/ሚኒስትሩ በህመም ገለል ማለት ጋር
ተያይዞ ስራቸውን ገትተዋል።

 

በዚህ ምክንያትም ካለፉት ሁለት ወራት ወዲህ ከፍተኛ ፕሮጀክቶችን የሚያንቀሳቅሱት እነዚህ ተቋማት በወሳኝ አካል እጦት ምክንያት ቀድሞ ከተጀመረ ሥራ ውጪ አዳዲስ ሥራዎችን ወስኖ ለማከናወን መቸገራቸውን ታውቋል፡፡

በቢሊየን ብር የሚገመቱ ፕሮጀክቶችን  እንዲያንቀሳቅሱ ተመስርተው ነገርግን በከፍተኛ የሰለጠነ የሰው ኃይል
እጥረት ምክንያት ብዙም መራመድ ያልቻሉት የባቡር፣የስኳር፣የብረታብረት ኮርፖሬሸኖች የጠ/ሚኒስትሩ መሰወር
በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ሆኖባቸዋል፡፡

በአምስት ዓመቱ ዕቅድ 10 አዳዲስ የስኳር ፋብሪካዎችን መገንባት ነባሮቹን አቅማቸውን ማሳደግ፣ሁለት ሺ ኪሎሜትር የባቡር መሰመር መዘርጋት፣24 የባቡር ሎኮሞቲቮችን ጨምሮ አገሪትዋ የሚያስፈልጋትን ማሸነሪዎች በመገጣጠም የቴክኖሎጂ ሸግግር ተጠቃሚ ለማድረግና የውጪ ምንዛሪ የማዳን ግብ ይዘው ቢቋቋሙም ባለፉት ሁለት የትራንስፎርሜሸን ዘመናት የረባና የሚታይ ሥራ ሳያከናውኑ ወደሶስተኛው ዘመን በሸግግር ላይ እንደሚገኙ ምንጫችን አስታውሰዋል፡፡

ስኳር ኮርፖሬሸን በ2004 በጀት ዓመት 20 ነጥብ 24 ቢሊየን ብር ከፍተኛ በጀት ተመድቦለት ከዚህ ውስጥ 18
ነጥብ 34 ቢሊየን ብር ለፕሮጀክቶቹ መድቦ እየተንቀሳቀሰ ቢሆንም ባለፉት ዓመታት ከዝግጅትና የሸንኮራ እርሻ
መሬት ከማዘጋጀት ያለፈ ሥራ አላከናወነም፡፡

የብረታብረት እና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሸን “ቢሾፍቱ” የተባሉ የአንበሳ ከተማ 400 ያህል አውቶቡሶችን ከቻይና
እያሰመጣ የገጣጠመና በሥራ ላይ ያሰማራ ቢሆንም ተሸከርካሪዎቹ በቴክኒክ ብቁ ባለመሆናቸው በየጊዜው በየመንገዱ
በብልሸት የሚቆሙ ሲሆን የተጣራ ነዳጅ የሚወስዱ በመሆናቸውና እሱን በአገር ውስጥ በቋሚነት የሚያቀርብ ኩባንያ
ካለመኖሩ ጋር ተያይዞ ከዚሁ በአጭር ጊዜ ከአገልግሎት ውጪ ሊሆኑ የሚችሉበት ችግር ተጋርጦባቸዋል፡፡

ምንም ዓይነት ልምድና ክህሎት ሳይኖር 24 የባቡር ሎኮሞቲቮችን ለማምረት የተያዘው ዕቅድም ለፕሮፓጋንዳ ተብሎ የተነገሩ ነው ብለዋል።

ከባቡር 2 ሺ ኪ.ሜ የመስመር መዘርጋት ዕቅዱ 800ኪ.ሜ ተጀምሮአል ቢባልም ከቅየሳ ያለፈ መሬት ላይ የወረደ
ሥራ አለመሰራቱን በአሁኑ ወቅት እየተሰራ ያለው የቀድሞ ኢትዮ- ጅቡቲ የባቡር መስመርን የማደስ ሥራ መሆኑን
ምንጫችን ጠቁሞ በዚህም ረገድ ከፍተኛ መጓተት መኖሩን ጠቅሷል፡፡

የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሸን ኤጀንሲ ከግብርና ሚኒስቴር በተለየ ዘርፉን በአዳዲስ ምርምር ለማሳደግ
በራሳቸው በአቶ መለስ ትዕዛዝ የተመሰረተ ሲሆን ኤጀንሲውን የሚመራ ዋና ዳይሬክተር ቢሾምም ቢሮውን በሰው ኃይልና
በማቴሪያል ከማጠናከር ሥራ ውጪ መራመድ አልቻለም፡፡ምንጮች እንደጠቆሙት በአሁኑ ሰዓት ቢሮው ከጠ/ሚኒስትሩ
መሰወር ጋር ተያይዞ ምንም ዓይነት ሥራ የለውም፡፡

____________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide