አርበኞች ግንቦት7 እና ኦብነግ በጋራ ለመታገል ተስማሙ

ግንቦት ፲ ( አሥር ) ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የአርበኞች ግንቦት7 የአንድነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄና የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻ አውጭ ግንባር በጋራ ባወጡት መግለጫ፣ ከግንቦት 7 እስከ ግንቦት9 ቀን 2009 ዓም በፍራንክፈርት ከተማ፣ በሁለቱም ድርጅቶች ተወካዮች አማካኝነት ባደረጉት ስብሰባ የህወሃት/ኢህአዴግ አገዛዝና የኢትዮጵያ ህዝብ ሰቆቃና ስቃይ እንዲያበቃ በጋራ ለመታገል፣ ሌሎች ዲሞክራሲ ሃይሎችን በማሳተፍ የኢትዮጵያ ህዝብ አማራጭ ሃይል እንዲያገኝ በግንባር ቀደምትነት ለመታገል ቃል መግባታቸውን ገልጸዋል።
ሁለቱም ድርጅቶች ተመጣጣኝ ውክልና ወደ አለበት ሃቀኛ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ለመሸጋገር የሚረዱ መሰረቶች ማኖራቸውንም ገልጸዋል።ሁለቱም ድርጅቶች ህወሃት/ኢህአዴግ ተወግዶ በኢትዮጵያ ውስጥ ዲሞክራሲያቂ የሽግግር ስርዓት እንዲፈጠር የሚፈልጉ እና የኢትዮጵያ ጉዳይ ይመለከተናል የሚሉ ወገኖች ወደ አንድ የጋራ መድረክ እንደሚጡ ለማመቻቸት በጋራ እንደሚሰሩ ገልጸው፣ ሌሎች ሃይሎችም እንዲቀላቀሉዋቸው ጥሪ አቅርበዋል።
የህወሃት/ኢህአዴግ አገዛዝ የፈጠረው ቀውስ ከኢትዮጵያ አልፎ ወደ ከፋ አካባቢያዊ ቀውስነት ሊያድግ እንደሚችል የሁለቱም ድርጅቶች ተወካዮች መገንዘባቸውንና ይህ አስጊ ሁኔታ በፍጥነት ካልተቀለበሰ ከፍተኛ ሰብአዊና ፖለቲካዊ ቀውስ በኢትዮጵያና አካባቢዋ እንደሚመጣ ስጋት እንዳደረባቸውም ገልጸዋል።
የአለማቀፉ ማህበረሰብም ትግሉን እንዲደግፍ ድርጅቶቹ ጠይቀዋል። የኢትዮጵያ የጦርና የፖሊስ ሰራዊት አባላት እንዲሁም የደህንነት መስሪያ ቤቱ ባልደረቦች ከህገወጡ የህወሃት አምባገነናዊ ስርዓት ጎን በመቆም ህዝብን ከመፍጀትና ከማሰቃየት ተግባር እንዲቆጠቡና ከህዝብ ጎን በመቆም ለውጥ ለማምጣት እንዲታገሉ ጥሪ አቅርበዋል።
አርበኞች ግንቦት7 ከኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ግንባር (ኦዴግ) ጋርም እንዲሁ በጋራ ለመታገል ስምምነት ላይ መድረሱ ይታወቃል። መቶ በመቶ በአንድ ፓርቲ የተሞላው የኢህአዴግ ፓርላማ አቦነግንና ግንቦት7 ትን አሸባሪ ብሎ መሰየሙ ይታወቃል። ይህን ተከትሎ በርካታ የኦብነግ አባላት በእስር ላይ ይገኛሉ።
የሁለቱ ድርጅቶች በጋራ ለመስራት መወሰን ትልቅ ስትራቴጂካዊና ፖለቲካዊ ፋይዳ እንዳለው ዘጋቢያችን አስተያየቱን አስፍሯል።