ብአዴን የሚያስተዳድራቸው ሰባቱ ድርጅቶች ኪሳራ ውስጥ ገብተዋል ተባለ

የካቲት ፫ ( ሦስት )ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በአማራ ክልል ብአዴን ያቋቋማቸው ከ16 በላይ የልማት ድርጅቶች ያሉ ሲሆን፣ 7ቱ በከፍተኛ ኪሳራ ውስጥ ናቸው። ድርጅቶቹ በመነሻ ካፒታል በአምስት ነጥብ ሰባት ቢልየን ብር ከህዝብ በጀት ተበድረው ቢቋቋሙም፣ የብአዴን ባለስልጣናት እንደልባቸው የሚዘርፏቸው ተቋማት መሆናቸውን ምንጮች ይገልጻሉ። ለዝርዝሩ ፋሲል የኔዓለም
በኮንስትራክሽን ፣ በማማከር ፣ በማሽነሪ ኪራይ ፣ በፋብሪካ ምርቶች ፣ በውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ እና በምርጥ ዘር አቅርቦት ዘርፎች ተሰማርተው እንዲሰሩ በብአዴን የተቋቋሙት ድርጅቶቹ፣ የተሰጣቸውን አላማ በመተግበር በኩል አፈፃፀማቸው ዝቅ ያለ እና ብአዴን ከመንግስት ካዝና የተበደረውን ገንዘብ እንኳን መመለስ እንዳይችል በኪሳራ ውስጥ መገኘታቸውን የብአዴን ከፍተኛ አመራር ከቦርድ አመራሮች እና ከአስተዳደር ኃላፊዎች ጋር በሚያካሂዱት ግምገማ ላይ ተገልጿል፡፡ ስብሰባውን የመሩት አቶ ገዱ አንዳርጋቸው እደተናገሩት ድርጀቶቹ እንደታሰበው በሀገር አቀፍ ደረጃ ተወዳድሮ መውጣት ይቅርና በክልሉ እንኳን አንድም ጠብ የሚል ስራ መስራት አልቻሉም ።
የድርጅቶቹ አመራሮች በበኩላቸው “ በመጪው ጊዜም ቢሆን ስኬታማ ስለመሆናችን እርግጠኞች አይደለንም፣ ስጋት ላይ ነን” ይላሉ ፡፡ “በአሁኑ ወቅት ገዢው ፓርቲ ወጣቱን ለማረጋጋት በሚል በሰጠው ልዩ ትኩረት፣ እኛ በተሰማራንበት ዘርፍ ውስጥ ወጣቶችን እያደራጀ እያስገባ ነው። ለነዚህ ወጣቶች በልዩ ድጋፍ ጫረታዎች የሚሰጡ ከሆነ እኛ የምንመራቸው ድርጅቶች እንዴት የታለመውን ትርፍ ሊያስመዘግቡ ይችላሉ ? “ በማለት የሚጠይቁት የድርጀቶቹ መሪዎች፣ “ ከዚያ ይልቅ የመከላከያ ኢንጀነሪንግ እና ኢፈርት እንደሚያደርጉት ሁሉ እኛ ትላልቅ ጫራታዎችን ካሸነፍን በሁዋላ፣ ስራውን ለእነሱ አከፋፍሎ መስጠቱ የተሻለ ሊሆን ይችላል” ሲሉ አስተያየተቻውን ይሰጣሉ።”
የአማራ ክልል ም/ፕሬዝዳንት አቶ ብናልፍ አንዷለም በበኩላቸው የልማት ድርጅቶችን የሚመሯቸው አካላት የብቃት ጉድለት አንቆ እንደያዛቸው በመናገር ለኩባንያዎች ኪሳራ አመራሮቹን ተጠያቂ አድርገዋል።
የአማራ ክልል የመንግስት የልማት ድርጅቶች ኃላፊ አቶ መጋቢያው ጣሰው ይህን አባባል በመቃወም “ የክልሉ መንግስት ድርጅቶቹ ሲወድቁ አሁን መጣ እንጅ፣ እስካሁን ድረስ ምንም አይነት እገዛ አድርጎ አያውቅም፡፡” በማለት ተጠያቂነቱን ወደ ብአዴን ከፍተኛ አመራሮች ገፍተውታል። ተቋማቱ የተቋቋሙበትን አላማ የመለየትና የመተግበር ችግሮች እንዳሉ ሆነው፣ ድርጅቶቹ በደረሰባቸው ኪሳራ የተነሳ ለሰራተኞቻቸው ደሞዝ መክፈል ሳይችሉ ቀርተዋል።
ብአዴን በመንግስት የልማት ድርጅት ስም ከሚመራቸው ተቋማት መካከል የከተሞች መንገድ ስራ ድርጅት፣ የውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ድርጅት፣ የውሃ ስራዎች ኮንስትራክሽን ስራ ድርጅት፣ ጢስ እሳት ውሃ ስራዎች ድርጅት፣ ሚሲግ የማሽነሪ ኪራይ፣ አማራ ደን ኢንትርፕራይዝ፣ የጎሽሜዳ ቧንቧና ፕላስቲክ ማምረቻ ፣ ጥቁር አባይ ትራንስፖርት አክሲዩን፣ አምባሳል ትሬዲንግ፣ በለሳ ሎጀስቲክ እና ትራንዚት አገልግሎት፣ ጥረት ኢንዶውመንት ስር ዳሸን ቢራ ፋብሪካ ፣ ዘለቀ እርሻ ልማት ፤ ጋፋት ኢንዶውመንት ፤ ጣና ሞባይል ፡ የአማራ ክልል ፕላስቲክ ፋብሪካ ፤ የገጠር መንገዶች ድርጅት ፤የኢትዮጵያ ቃጫ ውጤቶች ድርጅት መጋዘን፤ የኢትዮጵያ ማእድን ልማት አክሲዮን ማህበር፤ የባህርዳር ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ፣ የኮምቦልቻ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ፣ የግብርና መካናይዜሽን አገልግሎት ድርጅት፣ የትራንስፖርት ኮንስትራክሽን ዲዛይን አክሲዮን ማህበር እና ቪልቶ ሲራሮ እርሻ ልማት እና ዱከም ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ ይገኙበታል።
በልማት ድርጅቶቹ ስም የተቋቋሙት ኩባንያዎች ለብአዴን ባለስልጣናትና ለድርጅቱ ከፍተኛ የገቢ ምንጭ ሆነው ሲያገለግሉ፣ የመንግስትን ጫራታዎች ከገበያ ዋጋ ባነሰ በመውሰድ የህዝብ ሃብት ወደ ብአዴን እንዲገባ ሲያደርጉ ቆይተዋል።
በብአዴን ስም በሚመሩት ኩባንያዎች የህወሃት ድርጅት የሆነው ኢፈርት ከፍተኛ የአክሲዮን ድርሻ አለው።