ባለፈው ሳምንት በጎንደር በፈነዳው ቦምብ አንድ የውጭ አገር ዜጋን ጨምሮ አምስት ሰዎች መጎዳታቸው ተገለጸ

ኢሳት (ሚያዚያ 23 ፥ 2009)

የብሪታኒያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባለፈው ሳምንት በጎንደር ከተማ ደርሶ በነበረው የእጅ ቦምብ ፍንዳታ አንድ የውጭ ሃገር ዜጋን ጨምሮ አምስት ሰዎች መጎዳታቸውን ሰኞ ይፋ አድርጓል።

ይሁንና የብሪታኒያ መንግስት ጉዳት የደረሰበትን የውጭ ዜጋ ማንነት ከመግለጽ የተቆጠበ ሲሆን ዜጎቹ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ባሰራጨው የጉዞ ማሳሰቢያ አመልክቷል።

ባለፈው ሳምንት በጎንደር ከተማ የእንግዶች ማረፊያ ሆቴል ላይ የደረሰውን የቦምብ ፍንዳታ አስመልክቶ ኢሳት የአይን ዕማኞችን ዋቢ በማድረግ ዘገባ ማቅረቡም የሚታወስ ነው።

የብሪታኒያና የአሜሪካ መንግስታት በተከታታይ የቦምብ ፍንዳታ መድረሱን በማረጋገጥ ለዜጎቻቸው የጉዞ ማሳሰቢያን እያሰራጩ ይገኛል። በክልሉ እየደረሰ ያለው ጉዳት አካባቢውን በሚጎበኙ የውጭ ሃገር ቱሪስቶች ዘንድ ስጋት ማሳደሩም ይነገራል።