በፌደራል ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የባህርዳር ከተማ ተወካይ የነበሩት ወይዘሮ አዲሴ ዘለቀ አሟሟት አነጋጋሪ ሆኗል ።

ኅዳር ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻ / ኢሳት ዜና :- በባህር ዳር ከተማ  ሰፈነ ሰላም ክፍለ ከተማ ነዋሪ የነበሩትና የባህር ዳርን ህዝብ በመወከል በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲያገለግሉ የነበሩት ወይዘሮ አዲሴ ዘለቀ ባልታወቀ ሁኔታ በአዲስ አበባ ከተማ በትላንትናው እለት ማለትም ማክሰኞ ህዳር 6 /2009 ዓም. በጽ/ቤታቸው ሞተው ከተገኙ በሁዋላ ፣ ጉዳዩ የባህርዳርን ህዝብ እያነጋገረ ነው።

ወ/ሮ አዲሴ በፓርላማው በቆዩበት ወቅት ጠንከር ያሉ አስተያየቶችን መሰንዘር የሚታወቁበት ሲሆን በባህር ዳር ከተማ የክልሉ ምክር ቤት ጥቅምት 06/2009ዓም ባካሄደው ስብሰባ በፓርላማው ሳይፀድቅ ቀድሞ ስራ ላይ የዋለውን የወያኔን አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ  እንዲያጸድቀው የቀረበውን ሃሳብ ከተቃወሙት መካከል አንዷ ናቸው፡፡ወይዘሮ አዲሴ በዕለቱ የክልሉን ምክር ቤት አባላት በደስታ ያስጨበጨበ የተቃውሞ ንግግር ያደረጉ ሴት ተወካይ እንደነበሩ የቅርብ ጓዶቻቸው ተናግረዋል፡፡

ወ/ሮ አዲሴ ዘለቀ የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር የህዝብ ቅሬታ ሰሚ ጽ/ቤት ኃላፊ ሆነው በሰሩበት ጊዜ  አስተዳደራዊ ፍትህ ፈልገው የሚመጡ ባለ ጉዳዮችን በመቀበልና አፋጣኝ ምላሽ እንዲያገኙ በሁሉም መስሪያ ቤቶች አስተዳደራዊ ጥፋቶች እንዲሻሻሉና መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን የሚቀርቡ ቅሬታዎችን በማደራጀትና በመተንተን ትክክለኛ ምላሽ እንዲያገኙ ለማድረግ ሲሰሩ ነበር፡፡

የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር የህዝብ ቅሬታ ሰሚ ጽ/ቤት በህዝብ  የቀረቡትን ቅሬታዎች በትክክል መተግበራቸውን  ከማረጋገጥ ባሻገር አገልግሎት ሰጭ መስሪያ ቤቶች የተገልጋዩን እርካታ ለማስገኘት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ማድረግ እንዳለባቸው በጽኑ ሲታገሉ መቆየታቸውን የሚያውቁዋቸው ሰዎች ይናገራሉ። በወይዘሮ አዲሴ ድንገተኛ ሞት የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዎች  ቅሬታቸውን እየገለጹ ሲሆን ፤የሟች አስከሬን አለመመርመሩና በጥድፊያ እንዲቀበሩ መደረጋቸው ግለሰቧ የሞቱት በሰው እጅ ሊሆን ይችላል የሚል ጥርጣሬ በህዝቡ ላይ አሳድሯል፡፡

በክልሉ የሚገኙ ባለስልጣናት  የባህር ዳር ከተማ ተወካይ በድንገት በመሞታቸው ‹‹ለምን? ›› የሚል ጥያቄ ከማንሳትና የአስከሬን ምርመራ ከማድረግ ይልቅ የሃዘን መግለጫ ባነሮችን በማሰራት ለቀብር ሱሯሯጡ ታይተዋል፡፡ትናንት ህዳር 06/2009 በተወለዱ በ48 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ወ/ሮ አዲስ ዘለቀ የሁለት ልጆች እናት ነበሩ፡፡የቀብር ስነ-ስርዓታቸው በባህር ዳር ከተማ ድንባቄ መድሐኒዓለም ቤተክርስቲያን በርካታ የከተማዋ ህዝብ እና ወዳጅ ዘመዶቻቸው በተገኙበት ዛሬ ረቡዕ ከቀኑ በስድስት ሰዓት ተኩል ተፈጽሟል፡፡