በጣና ሃይቅ ዳርቻ በሚገኙ ከተሞች የመሬት ቅርምቱ ጨምሯል

ሰኔ ፲፪( አሥራ ሁለት ) ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ወጣቶች በተወለድንበት ምድር ነጻነት አጥተናል ይላሉ
በጣና ሃይቅ ዳርቻ በሚገኙ በጎርጎራ ፣ቁንዝላና ባህርዳር ከተሞች ዙሪያ የሚገኙ ነዋሪዎች እንደተናጉሩት “ የጣና ሃይቅ አካባቢ በልማት ስም ተሸንሽኖ በመሰጠቱና ለአመታት ያለምንም ስራ ታጥረው በመቀመጣቸው ህዝቡ እየተቸገረ ነው።
በጎርጎራና ዙሪያዋ ለ23 ዓመታት ታጥረው የተቀመጡ ቦታዎች አሉ። አርሶአደሮች የእርሻ መሬት አጥተው በችግር ላይ ናቸው። ወላጆች ልጆቻቸውን ማስተዳደር አልቻሉም፣ የሚሉት ነዋሪዎች፤ ባለሃብት ተብለው ቦታውን የተቀራመቱት ሰዎች ከሰል እያከሰሉ ከመሸጥ ውጭ የረባ ስራ አለመስራታቸውንም ይናገራሉ።
ወጣቶች በገዛ መሬታችን ነጻነታችንን አጣን እያሉ እየተቃወሙ መሆኑን የሚገልጹት ነዋሪዎች፣ ችግሩ እየከፋ በመሄዱ አስቸኳይ መፍትሄ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።