በጎንደርና ባህርዳር ከተሞች ባለፈው ሳምንት የደረሰውን የቦምብ አደጋ ተከትሎ ውጥረት መንገሱ ተገለጸ

(ጥር 9 ፥ 2009)

ሰሞኑን በጎንደርና ባህርዳር ከተሞች የደረሰን የቦምብ አደጋ ተከትሎ በሁለቱ ከተሞች ውጥረት መንገሱን የብሪታኒያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ማክሰኞ ገለጸ።

የጥምቀት በአል አከባበርን አስመልክቶ በሁለቱ ከተሞች ተጨማሪ ጥቃት ሊደርስ ይችላል ሲል ፖሊስ ማሳሰቢያ መስጠቱንም የብሪታኒያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለዜጎቹ ባሰራጨው የጉዞ ጥንቃቄ መረጃ አመልክቷል።

ይሁንና ፖሊስ ሊደርስ ይቻላል ስላለው ተጨማሪ ጥቃት የሰጠው ዝርዝር መረጃ የሌለ ሲሆን፣ በሁለቱ ከተሞች ከነገ ረቡዕ ጀምሮ የሚከበረውን የጥምቀት በአል አስመልክቶ ቁጥሩ ከፍተኛ የሆነ የጸጥታ ሃይል መሰማራቱ ታውቋል።

የብሪታኒያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከዚህ ቀደም ዜጎቹ ወደ አካባቢው በሚደረጉት ጉዞ ላይ የጥንቃቄ ዕርምጃን እንዲወስዱ የሰጠው ማሳሰቢያም ተግባራዊ ሆኖ እንደሚቀጥል በመግለጫው አስፍሯል።

ከአንድ ሳምንት በፊት በሁለቱ ከተሞች በሚገኙ ሆቴሎች የቦምብ አደጋ መድረሱ የሚታወስ ሲሆን፣ በጎንደር ኢንታሶል ሆቴል በደረሰው ፍንዳታ የአንድ ሰው ህይወት አልፎ 18 ሰዎች ጉዳት እንደደረሰባቸው ፖሊስ ገልጿል።

ይሁንና የከተማዋ ነዋሪዎች እንዲሁም የብሪታኒያ መንግስት በቦምቡ አደጋ ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች ስድስት ብቻ መሆናቸውን ባወጡት መግለጫ አመልክተዋል። ፖሊስ ጥቃቱን አድርሰዋል የተባሉ ሰዎችን ለመያዝ ፍለጋ እያካሄደ እንደሆነ ቢገልጽም እስካሁን ድረስ የተያዘ ተጠርጣሪ ይኑር አይኑር የተግለጸ ነገር የለም።

ካለፈው አመት ሃምሌ ወር ጀምሮ በሰሜን ጎንደር ዞን ስር በሚገኙ የተለያዩ አካባቢዎች የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ በተለይ በጎንደርና ባህር ዳር ከተሞች አለመረጋጋት መስፈኑን የተለያዩ አካላት በመግለጽ ላይ ናቸው።

ይኸው አለመረጋጋት በተለይ በሁለቱ ከተሞች የደረሰውን የቦምብ አደጋ ምክንያት በማድረግ ተባብሶ እንደሚገኝ የብሪታኒያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አክሎ ገልጿል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ረቡዕ እና ሃሙስ አዲስ አበባ ከተምን ጨምሮ በተለያዩ ክልሎች የሚከበረውን የጥምቀት በአል አስመልክቶ የጸጥታ ቁጥጥር እንዲጠናከር መደረጉን ማክሰኞ አስታወቀ።

የከተማዋ ነዋሪዎች በበኩላቸው የበአሉን ዝግጅት አስመልክቶ የጸጥታ ሃይሎች ተሽከርካሪዎችን በማስቆም ፍተሻ በማካሄድ ላይ መሆናቸው ገልጸዋል። በአሉ በሰላም እንዲከበር ለማድረግ በርካታ የጸጥታ ሃይል በተለያዩ የአዲስ አበባ ስፍራዎች እንዲሰማራ መደረጉን ኮሚሽኑ ለመገናኛ ብዙሃኑ ባሰራጨው መግለጫው አመልክቷል።

በከተማዋ በሚገኙ የተለያዩ አካባቢዎች ፍተሻ ተጠናክሮ መቀጠሉን የሚናገሩት ነዋሪዎች በበኩላቸው በተያዘው አመት በአሉን አስመልክቶ የተደረገው የጸጥታ ቁጥጥር ከመቼውም ጊዜ የተለየ መሆኑን ይናገራሉ።

የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የጸጥታ ቁጥጥሩ እንዲጠናከር የተደረገው የከተራና የጥምት በአልን በሰላም እንዲከበር ለማድረግ እንደሆነ ገልጿል።