በግብር ትመና ላይ የተነሳው ተቃውሞ ዛሬም ቀጥሏል

(ኢሳት ዜና –ሐምሌ 18/2009)በመንግስት በኩል የሚሰጡት የተምታቱ መግልጫዎች አነጋጋሪ ሆነዋል።የጋቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዳይሬክተር አቶ ከበደ ጫኔ በ24 ሰአት ልዩነት ሁለት ተቃራኒ መግለጫዎችን ሰጥተዋል።

እሁድ ለንባብ በበቃው ሪፖርተር ጋዜጣ የተናገሩት አቶ ከበደ ጫኔ ነጋዴው የፈለገውን የአቅሙን እንዲከፍል ውሳኔ ላይ ተደርሷል ብለዋል።

በማግስቱ ይህን ሀሳባቸውን በመሻር የተተመነውን ግብር ነጋዴው የከፍላል ሲል ገልጸዋል።ተቃውሞው ወደ አጠቃላይ ህዝባዊ አመጽ የሚሸጋገር ከሆነ የግብር ተመኑ ሊሻር ይችላል የሚል ውሳኔ በመንግስት ጠረጴዛ ላይ ተቀምጦ ሁኔታዎ እየተገመገሙ እንዳሉም መረጃዎች ይጠቁማሉ።

እስከዛው ነጋዴውን ነጥሎ በመምታት አስተባባሪዎችን የመለየትና የማሰር እርምጃዎች እንዲወሰዱ በህወሃት መንግስት በኩል ውሳኔ ላይ እንደተደረሰና ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑም ታውቋል።

ምንም እንኳን በህወሃት መንግስት በኩል የተምታቱ መግለጫዎች መሰጠታቸው ቢቀጥልም ማስፈራራትና የሃይል እርምጃዎችን ቢወስድም የስራ ማቆም አድማው ግን ተጠናክሮ መካሄዱን ቀጥሏል።

በአዲስ አበባ ከተለያዩ አካባቢዎች የደረሱን መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ከህወሃት የደህንነት የፖሊስ ሃይሎች የተፋጠጡ ነጋዴዎች በአድማው እንደቀጠሉ ናቸው፡፡

በመርካቶ የተወሰኑ መደብሮች በግዳጅ እንዲከፍቱ ቢደረጉም በአብዛኛው ሱቆችና መደብሮች በአድማው መቀጠላቸውን ለማወቅ ተችሏል።

ዛሬ በላፍቶ፣ቄራና ተክለሃይማኖት በርከት ያሉ የንግድ ቤቶች ተዘግተው እንደነበር ያገኘንው መረጃ ያመለክታል።

በተክለሃይማኖት የመኪና መለዋወጫ መደብሮች በከፊል ተዘግተው የዋሉ ሲሆን አንዳንዶቹም በራቸውን ገርበብ አድርገው ከስራ ውጪ በመሆን ሁኔታዎችን ሲከታተሉ እንደነበር የአይን እማኞች ገልጸዋል።

በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 6 ቄራ የሚገኘው የገበያ አዳራሽ ያሉ ሱቆች ዛሬ አድማውን መቀላቀላቸው ተሰምቷል።

በገበያ አዳራሹ የሚሰሩ ነጋዴዎች አንድ አይነት አቋም ይዘው ሱቆቻቸውን መዝጋታቸው የታወቀ ሲሆን ፖሊስ ወዲያውኑ አካባቢውን እንደከበበው ተገልጿል።

የተዘጉትን ሱቆችና መደብሮች ለማስከፈት በመንግስት ታጣቂዎች መጠነ ሰፊ የሃይል እርምጃ በመውሰድ ላይ መሆኑንም ዘገባዎች ያመለክታሉ።

አራተኛ ፖሊስ ጣቢያና እድገት በሚባሉ አካባቢዎች ፖሊስና ነጋዴው ተፋጠው እንደነበርም ታውቋል።

ዘግይቶ በደረሰን ዜናም የተወሰኑትን ፖሊስ ማሰሩ ታውቋል።

በአዲስ አበባ የህወሃት መንግስት ነጋዴውን በሃይል ለማንበርከክ የከፈተውን ዘመቻ አጠናክሮ የቀጠለ መሆኑን ማምሻውን የደረሱን መረጃዎች አመልክተዋል።

የማስፈራሪያ ደብዳቤ በተዘጉ ሱቆችና መደብሮች ግድግዳዎች ላይ የተለጠፉ ሲሆን የታሸጉ እንዳሉም ለማወቅ ተችሏል።

በተያያዘ ዜና በአማራ ክልል በብቸና፣ሞጣና ሸበል በረንታ የተጀመረው የነጋዴዎች የስራ ማቆም አድማ እንደቀጠለ ነው።

በተለይ በሸበል በረንታ የደውሃ አድማ አምስተኛ ቀኑን ያስቆጠረ ሲሆን ሰባት ነጋዴዎች መታሰራቸውን የአካባቢው የኢሳት መረጃ ምንጭ ገልጿል።

የነጋዴዎቹ መታሰር ይበልጥ ቁጣን የቀሰቀሰ ሲሆን ህብረተሰቡም በመቀላቀል በአድማው እንቅስቃሴ አንድ ላይ ሆኖ ተቃውሞውን እያሰማ ነው ተብሏል።