በጂጂጋ የተደረገው የጦር አዛዦች ስብሰባ በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል የሚደረገው ዘመቻ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ውሳኔ አሳለፈ

ጥር ፩ (አንድ)ቀን ፳፻ / ኢሳት ዜና :- ባለፈው ሳምንት በጂጂጋ ከተማ በተደረገው  የከፍተኛ የጦር አዛዦች ስብሰባ ላይ በሰሜን ጎንደር የሚደረገውን ተቃውሞ ተከትሎ መወሰድ ስለሚገባቸው እርምጃዎች ውሳኔዎችን አሳልፏል።

የምእራብ እዝ ማሰልጠኛ ሰሜን ጎንደር በሚገኘው ሰራባ በሚባለው ቦታ ላይ እንዲሆን የመጨረሻ ውሳኔ  በደቡብ ምስራቅ እዝ በ13ኛ እና 32ኛ ክፍለ ጦሮች ስር የሚገኙ ሁለት ሬጀመንት ጦር ወደ ሰሜን ጎንደር በማምጣት፣ ሰሜን ጎንደርን ሙሉ ለሙሉ የወታደራዊ ቀጠና አድርጎ የተነሳውን የህዝብ ተቃውሞ መደምሰስ የሚል ውሳኔም አሳልፏል።

እንዲሁም በጭልጋ የሚቋቋመውን አንድ አዲስ ክፍለ ጦር በፍጥነት አደራጅቶ ወደ እንስቃሴ እንዲገባ የማድረግ ስራን ተቀላጥፎ ይቀጥል ብሎአል። ይህን ተግባር ለማከናወን ለሚቋቋመው አዲስ ክፍል ጦር የሚሆን ሰራዊት ከተለያዩ የጦር ክፍሎች እንዲዋጣ እንዲሁም ታህሳስ 25 ከብር ሸለቆ የተመረቁ 400 የሚሆኑ አዲስ ምልምል ወታደሮች ጭልጋ ላይ በሚቋቋመው ክፍለ ጦር ሰር እንዲጠቃለሉ የተወሰነ መሆኑ ታውቋል።

የሰራዊቱን አለመታዘዝ ሌላው አጀንዳ የነበረ ሲሆን፣ በተለያዩ የጦር ክፍሎች የሚገኙ ወታደሮች አልታዘዘም እያሉ ማስቸገራቸው   ከፍተኛ ስጋት ላይ  እንደጣላቸው  የተለያዩ ከፍተኛ የጦር አዛዦች ተናግረዋል። ሰራዊቱ እየከዳን ስለሆነ አፋጣኝ እርምጃዎች ካልተወሰዱ የከፋ አደጋ ውስጥ ልንገባ እንችላለን የሚሉት የጦር አዛዦች ፣ ሰራዊቱ የሚሰጠውን ግዳጅ በአግባቡ እንዲወጣ ለማድረግ የደሞዝ ጭማሪ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን  ወስኗል።

በ32ኛ ክፍለ ጦር ስር የሚገኝ አንድ ሻምባል ጦር የገባበት አለመታወቁም በስብሰባው ላይ ተነስቶ ነበር። በዚህ ሚስጢራዊ ስብሰባ ላይ ከተገኙት መካከል ኢታማጆር ሹሙ  ጄ/ል ሳሞራ የኑስ፣ የአየር ሃይል አዛዥ ሌ/ጄ አደም መሃመድ፣ የወታደራዊ መረጃ ዋና መምሪያ ሃላፊ  ሚ/ር ገብሬ አዳህነ (ዲላ) ፣ የመከላከያ ዩኒቨርስቲ ኮማንዳንት ሜ/ጄኔራል ሃለፎም እጅጉ ፣ የደቡብ ምስራቅ እዝ ዋና ዛዥ ሌ/ጄ አብርሃም ወ/ማርያም ( ኳርተር) እንዲሁም  የም/እዝ ዋና አዛዥ ሜ/ጄ ፍሰሃ ኪዳኑና ሌሎችም ቁልፍ የመከላከያ አዛዦች ተገኝተዋል።

ስበሰባውን ተከትሎ በዚህ ሳምንት ውስጥ በጎጃምና ጎንደር አካባቢዎች የተጠናከረ የአሰሳ ስራ  እንዲደረግ ውሳኔ ማሳለፉን የመከላከያ ምንጮች ገልጸዋል።