በወልድያ ከተማ የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች የስራ ማቆም አድማ አደረጉ

ኢሳት (የካቲት 23 ፥ 2008)

በወልድያ ከተማ የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች የስራ ማቆም አድማ እያደረጉ እንደሆነ ከስፍራው የደረሰን ዜና አመለከተ።

ከወሎ ወልዲያና ወደተለያዩ ከተሞች የሚደረገው የትራንስፖርት አገልግሎት እንደ ኢትዮጵያ ሰዓት አቆጣጠር ከ10 ሰዓት ጀምሮ መቋረጡን ለኢሳት የደረሰ መረጃ ያስረዳል።

በአድማው ከአሽከርካሪዎች በተጨማሪ የተሽከርካሪ ባለንብረቶችም ተቀላቅለዋል ተብሏል።

የመንግስት ካድሬዎች ሾፌሮችንና የተሽከርካሪ ባለቤቶችን እያስፈራራ ቢሆንም፣ ከባህርዳር ደብረታቦርም ጭምር አድማው ሊስፋፋ እንደሚችል እየተነገረ እንደሆነ የኢሳት ምንጮች ከወልዲያ አረጋግጠዋል።

ተግባራዊ የሆነው የትራፊክ መመሪያ አዋጅና የነዳጅ ዋጋ መጨመርን ምክንያት በማድረግ በአዲስ አበባ የተነሳው አድማ በኦሮሚያ ክልል በተለይም በባሌ ሮቤ አዲስ አበባ ዙሪያና አምቦ የቀጠለ ሲሆን ከአንድ ወር በፊትም በሆሳዕና መካሄዱ ይታወሳል።

መመሪያው ሃገር አቀፍ በመሆኑ ተቃውሞው በተለያዩ አካባቢዎች እንደሚካሄድ መረጃዎች ያሳያሉ። ይህንን ጉዳይ በተመለከተ ኢሳት አዳዲስ መረጃዎችን እየተከታተለ ለህዝብ የሚያቅርብ መሆኑን እንገልጻለን።