በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የተፈናቀሉት ዜጎች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ መሆናቸው ታወቀ

(ኢሳት ዜና–ጥቅምት 8/2010)በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በተፈጠረው ግጭት የተፈናቀሉት ዜጎች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ መሆናቸውን መንግስት አስታወቀ።

ከተፈናቀሉት ውስጥ ከ100 የሚበልጡ እናቶች ድንኳን ውስጥ ልጆቻቸውን መገላገላቸውን የመንግስት ቃል አቀባይ ዶክተር ነገሬ ሌንጮ ይፋ አድርገዋል።

የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችም በችግሩ ሳቢያ የአንዱ ክልል ተማሪ ወደ ሌላው ክልል ዩኒቨርስቲ ሄዶ ለመማር እንደማይፈልግም ተመልክቷል።

የመንግስት ቃልአቀባይ ዶክተር ነገሬ ሌንጮ ማክሰኞ ዕለት ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ እንዳመለከቱት በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የሚመራ የልኡካን ቡድን ተፈናቃዮቹን ለመጎብኘት በድሬደዋና በሀረር በተንቀሳቀሰበት ወቅት የችግሩን ስፋት መረዳቱን ገልጸዋል።

በግጭቱና በተከተለው መፈናቀል ወላጆች ከልጆቻቸው ጋር መለያየታቸውንና አለመገናኘታቸውን፣በጥቃቱ ጉዳት የደረሰባቸውን ሴቶች ጭምር መመልከታቸውን ተናግረዋል።

በድሬደዋና ሀረር በተፈናቃዮች ካምፕ 106 እናቶች ልጆቻቸውን መገላገላቸውን ገልጸዋል።

ቀውሱ ከተገመተው በላይ እንደሆነ በመናገርም የአጠቃላይ ተፈናቃዮች ቁጥር በመቶ ሺዎች እንደሚቆጠርም አመልክተዋል።

በኦሮሚያና በሶማሌ ክልል በተፈጠረው በዚህ ግጭት ሳቢያም የአንዱ ክልል ተወላጅ ወደሌላው ክልል ዩኒቨርስቲ ሄዶ ላለመማር ጥያቄ እያቀረቡ መሆናቸውንም ዶክተር ነገሬ ሌንጮ ገልጸዋል።

ሰው ከሀገሩ አልፎ ሌላ ሀገር ሔዶ በሚማርበት ዘመን በአንድ ሀገር በአንድ ባንዲራ ስር የምንኖር ሰዎች እዚህ ሁኔታ ውስጥ መድረሳችን ያሳዝናል ሲሉም ገልጸዋል።

ብሔራችንን ከማወቃችን በፊት እኮ ሰዎች መሆናችንን ማወቅ ነበረብን ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

ሆኖም ዶክተር ነገሬ ሌንጮ ሁኔታዎችን ወደዚህ ስለገፋው ስለስርአቱ ፖሊስ ምንም አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለም በቅርቡ በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘውን የሶማሌ ላንድ ጉዳይ ፈጻሚ ጽሕፈት ቤትን ያቃጠለው ከሶማሌላንድ በቅርቡ የተፈናቀለ ኢትዮጵያዊ መሆኑን ፖሊስ ገልጿል።

ከሳምንት በፊት በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 3 የሚገኘውን የሶማሌላንድ ጉዳይ ጽሕፈት ቤት በማቃጠል የተጠረጠረውና በቁጥጥር ስር የዋለው ግለሰብ በቅርቡ ከሐርጌሳ ሶማሌላንድ ተፈናቅሎ የወጣ መሆኑም ተመልክቷል።

የኦሮሚያና የሶማሌ ድንበር አዋሳኝ ግጭትን ተከትሎ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን የኦሮሞ ተወላጆች ከጎረቤት ሀገር ሶማሌላንድ ሐርጌሳ መፈናቀላቸው ይታወሳል።

ቃጠሎው ከ45 ደቂቃ በላይ የፈጀና በእሳት አደጋ ሰራተኞች ርብርብ የጠፋ መሆኑንም ፖሊስ አስታውቋል።