በእስር የሚገኙ የኦፌኮ መሪዎች የአውራ ፓርቲ አስተሳሰቦች ለቀው አዲስ ስርዓት እንዲፈጠር መግለጫ አወጡ

ሰኔ 21 ፥ 2009

በእስር ቤት የሚገኙት የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ/ ኦፌኮ/ መሪዎች የአብዮታዊ ዲሞክራሲ የልማታዊ መንግስትና የአውራ ፓርቲ አስተሳሰቦች ቦታ ለቀው አዲስ ሥርዓት እንዲፈጠር በመጠየቅ መግለጫ አወጡ። 

የድርጅቱን ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ በእስር ላይ የሚገኙት የኦፌኮን መሪዎች አሁን በስልጣን ላይ ያለው አገዛዝ በተሐድሶ ስም የሚያደርገው እንቅስቃሴ ተግባራዊ የማይሆንና ሕዝብን ለመደለል የሚደረግ ሙከራ ነው ብለዋል።

እስረኞቹ “በአሮጌ አቁማዳ አዲስ የወይን ጠጅ አይጨመርም” በሚል ያወጡት መግለጫ እንደሚያመለክተው ጥልቅ ተሐድሶ በሚል በገዥው ፓርቲ የሚሰበከው አስተሳሰብ ተግባራዊ ሊሆን የማይችልና የነበረውን የሚደግም እንቅስቃሴ ነው ብለዋል።

የሀገሪቱ ተቋማት ማለትም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዋና ኦዲተር፣ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽንና የፀረ ሙስና እንዲሁም የእንባ ተቋማት ጠባቂ መስሪያ ቤቶች አደረጃጀታቸውና አፈጣጠራቸው በኢህአዴግ አስተሳስብ የቃኙ በመሆኑም ፋይዳ የላቸውም ብሏል መግለጫው።

ተቃዋሚዎችን በገፍ በማሰርና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በመደንገጉ የሕዝብን እንቅስቃሴ ማፈን እንደማይቻልም በእስር ቤት የሚገኙ የኦፌኮ አመራሮች በመግለጫቸው አስታውቀዋል።

ባለፉት 26 የአገዛዝ ዓመታት ሕዝቡ ላይ ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ረገጣ፣ የኢኮኖሚ ዘረፋና የፖለቲካ ጭቆና የተፈፀመ መሆኑንም መግለጫው አስታውሷል።

በተለይ ደግሞ ከሕዝብ ተቃውሞ ጋር በተያያዘ የፖለቲካ መፍትሄ ከመሻት ይልቅ በተወሰደው የኃይል እርምጃ አገዛዙ በሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች እንደሞቱ እንዲታሰሩ እና ከፍተኛ ግፍና ሰቆቃ እንዲፈፀምባቸው አድርጓልም ብለዋል።

በጥልቅ ተሐድሶ ስም የሚስተካከል ነገር ስለማይኖር በስልጣን ላይ ያለው አምባገነን መንግስት ስለተቀየረ መፍትሄ እንደማይኖርና ትግሉም እንደሚቀጥል መግለጫው አሳስቧል።

በሽብርተኝነትና አመፀ በመቀስቀስ ተከሰው በእስር ላይ የሚገኙት የኦፌኮ አመራሮች ጉዳያቸው በፍርዱ ሂደት ላይ ቢሆንም እስካሁን ድረስ በቀጠሮ መራዘም ምክንያት ውሳኔ እንዳላገኙ ይታወቃል።