በአገር ሽማግሌ ስም መቀሌ ከሄዱት መካከል 4ቱ የተባረሩ የአርበኞች ግንቦት አባላት የነበሩ ናቸው

ሐምሌ ፳ ( ሃያ ) ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ከድርጅቱ ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው የአማራ እና የትግራይን ህዝብ እናስታርቃለን በማለት ወደ መቀሌ ከተጓዙ፣ የአገር ሽማግሌ ስም ከተሰጣቸው ሰዎች መካከል አራቱ በአርበኞች ግንቦት7 ስር ተደራጅተው ሲሰሩ የነበሩና በሁዋላ ላይ ህወሃት በሰላይነት እንዲያገለግሉት እንደመለመላቸው ሲታወቅ የተባረሩ ናቸው።
አቶ ታያቸው ጥሩነህ፣ አቶ ሞላ መኮንን፣ አሰማራው መኮንን እና ሻንቆ ሽባባው የተባሉትን በመድረክ ላይ ይናገሩት የነበሩት በመጀመሪያ ለነጻነት ትግሉ ዋና ተዋናይ ሆነው ከቀረቡ በሁዋላ የተሰጣቸውን ህዝባዊ አደራ በመተውና የድርጅት ዲሲፕሊን በመጣስ ለህወሃት መረጃ ሲያቀብሉ የነበሩ መሆናቸውና ሲደርስባቸው በማምለጥ ከድርጅቱ የተባበሩ መሆናቸውን ንቅናቄው ገልጿል። ግለሰቦቹ በአሁኑ ሰአት ከፍተኛ ገንዘብ ተመድቦላቸው ከደህንነት አባላት ጋር “ምህረት እናሰጣላን” በማለት ታጋዮችን በማታለል ለአገዛዙ እጃቸውን እንዲሰጡ ለማድረግ እየሰሩ ነው ብሎአል።
ለግለሰቦቹ ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው የገለጸው ድርጅቱ፣ አሁን ደግሞ “ የአማራ ህዝብ ወኪል ነን” በማለት በቴለቪዥን እየተናገሩ ነው ይላል። ህዝቡ እነዚህን ግለሰቦች በከሃዲነት በመቁጠር እንዲያገላቸው ድርጅቱ ጠይቋል።
የህወሃትን የበላይነት ለመቀደስ መቀሌ የተገኙት በአገር ሽማግሌ ስም የተመረጡት ሰዎች፣ አብዛኞቹ ያገዛዙ ደጋፊዎች ወይም አባላት ናቸው። ከወልድያ ከተማ ከተመረጡት 20 ሰዎች መካከል ብዙዎቹ የአገዛዙ ደጋፊዎች መሆናቸው በከተማው ህዝብ ዘንድ በደንብ እንደሚታወቅ ወኪላችን ገልጿል። ከእነዚህ መካከል አቶ ጌታቸው ሃይሌ ቤቶችን እየሰራ የሚሸጥ ባለሃብት የብአዴን አባል፣ ወሰን መርሶ የብአዴን አባልና በከተማው በስልጣኑ ተመክቶ ህንጻ የገነባ፣ አቶ አህመድ የመቻሬ ሆቴል ባለቤት የኢህአዴግ አባል፣ አቦይ ጸጋዬ የቀበሌ የጁገነት ማህበራዊ ዳኛ የህወሃት አባል መሆናቸውን ወኪላችን አክሎ ገልጿል።
አገዛዙን ይደግፋሉ ተብለው ከገቡት የአገር ሽማግሌዎች መካከል ሁለቱ ለኢሳት በሰጡት መረጃ፣ አጠቃላይ ሁኔታው ህወሃት ወታደራዊ ጉልበት እንዳለው ለማሳየት የተጠቀመበት ዝግጅት እንደነበር ገልጸዋል። ሂደቱን እንደማያምኑበት የሚገልጹት እነዚህ ግለሰቦች፣ የክልሉ ህዝብም ድርጊታቸውን ቁም ነገር አለው ብሎ እንዳልወሰደውና ለቴሌቪዥን ፍጆታ ካልሆነ በስተቀር ምንም የሚመጣ ለውጥ እንደሌለ ገልጸዋል።