በአዲስ አበባ ዙሪያ የተፈናቀሉ አርሶ አደሮች ብሶታቸውን አሰሙ

መጋቢት ፳፫( ሃያ ሦስት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ከነባር እራሻ መሬታቸው የተፈናቀሉ አርሶአደሮች በቂ ያልሆነ ካሳ ሳይከፈላቸው ከቀያቸው በመነሳታቸው ሳቢያ በራሳቸውና በቤተሰቦቻቸው ላይ የደርሰባቸውን አስከፊ ሰቆቃ የአዲስ አበባ መስተዳድር በጠራው ስብሰባ ላይ በምሬት ተናግረዋል።
መንግስት ትንሽ ቦታ እንኳን ሳይሰጣቸው ከይዞታቸውን እንዲነሱ በመደረጋቸው ለአስከፊ ሕይወት መዳረጋቸውንና ለወደፊቱም ልጆቻችንን ምን እናብላቸው? እንደ እቃ ሜዳ ላይ ተጥለናል ሲሉ ተፈናቃይ አርሶ አደሮቹ ያጋጠማቸውን የሕይወት ተግዳሮቶች በስብሰባው ላይ አሰምተዋል።
ለአስር ዓመታት ተብሎ የተሰጣቸው ካሳ አግባብ እንዳልሆነ ጠቅሰው፣ ከአስር ዓመታት በኋላስ ገበሬ በምድር ላይ የለም ወይ እባካችሁ መፍትሔ ስጡን? ሲሉ አንድ አርሶአደር ብሶታቸውን ገልፀዋል።
አንድ ካሬ ቦታ በ29 ብር ሒሳብ ተተምኖ የተሰጣቸው ክፍያ አግባብ አለመሆኑን ከአንድ ኪሎ ምስር ባነሰ ዋጋ መሬታቸውን መነጠቃቸውንና እንጀራ ስንበላ የነበረው ዛሬ ቆሎ ለመብላት የማንችልበት ደረጃ ላይ ደርሰናል ብለዋል።
የማዘጋጃ ቤት ኃላፊዎች የያዛችሁት ይዞታ ትርፍ ነው መሬት ነዳጅ ነው ለገበሬ ልጅ አታስቡ። መባላቸውንና ችግራቸውን ሰሚ አካል ማጣቸውንም ተፈናቃይ አርሶአደሮቹ አክለው ተናግረዋል። ዘገባውን በቅድሚያ ያቀረበው ሸገር ሬዲዮ ነው፡፡