በአማራና ኦሮምያ ክልሎች አዲስ የእስር ዘመቻ ተከፈተ

ጥር ፩ (አንድ)ቀን ፳፻ / ኢሳት ዜና :- የኢሳት ምንጮች እንደገለጹት በሳምንቱ መጨረሻ በኦሮምያ በተለይም በአዳማ ፣ ጉጂ እና ቦረና ዞኖች፣ በአማራ ክልል ደግሞ በጎንደር እና አዊ ዞኖች በርካታ ወጣቶች ተይዘው ታስረዋል።

10 ሺ ወጣቶች ከእስር መፈታታቸውን ባስታወቀ ሁለት ሳምንት ባልሞላው ጊዜ ውስጥ አዲስ የተጀመረው የእስር ዜና በነዋሪዎች ላይ ጫና እየፈጠረ ነው። በአማራ ክልል በተለይ ከወራት በፊት ተደርጎ በነበረው ህዝባዊ አመጽ ላይ በህወሃት ደጋፊዎች ላይ ጥቃት አድርሰዋል በሚል የተጠረጠሩ ወጣቶች እየተፈለጉ የታሰሩ ሲሆን፣ ሌሎች ደግሞ ክትትል እየተደረገባቸው ነው። የህወሃት ካድሬዎች በክልሉ በብዛት በመሰማራትና ለአንዳንድ የአካባቢው ተወላጆች  ገንዘብ በመስጠት እንዲሁም ሹመት ይሰጣችሁዋል በሚል ፣ ጸረ ህወሃት አቋም ያላቸውን ወጣቶች እንዲጠቁሙ እያግባቡ ነው።

በአዳማ፣ ጉጂና ቦረና ዞንም እንዲሁ አፈሳው ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፣ ወላጆች ልጆቻቸውን እንዲያመጡ ጫና እየተደረገባቸው ነው። እንደ አዲስ ነውጥ ሊያነሱ ይችላሉ የተባሉ ወጣቶችን በተናጠል እየለዩ ከመኖሪያ ቤታቸው፣ ከስራ ገበታቸው እና ከትምህርት ቤቶች አፍነው በመውሰድ ማሰሩ ተጠናክሮ መቀጠሉን ምንጮቻችን ገልፀዋል። ከኢሬቻ የጅምላ ግድያ በኋላ አብዛኛኛው ሟቾች  እና ቁስለኞች የአካባቢው ነዋሪዎች መሆናቸውን ተከትሎ የህወሃት ኢህአዴግን አገዛዝ የሚያወግዙ ወጣቶች በተለያዩ መንገዶች ተቃውሟቸውን እየገለጹ ነው። ከቀድሞው በተለየ ሁኔታ በአካባቢው ነዋሪዎች ተቀባይነት ያጣው ገዥው ህወሃት ኢህአዴግ በክልሉ ውስጥ አፈናውን ካጠናከረባቸው አካባቢዎች ውስጥ የምስራቅ ሸዋ ዞን በቀዳሚነት ይጠቀሳል።

በምስራቅ ሸዋ ዞን ውስጥ የሚገኙ ወጣቶችን ፀጉራቸውን በመላጨት ክብር በሚነካ ሁኔታ ”አይደገምም” የሚል ቲሸርት በማልበስ የተወሰኑ ወጣቶች ከእስር የተለቀቁ ቢሆንም፣  አሁንም በታንከኛ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ካምፕ፣ በፖሊስ ጣቢያዎች እና በተለያዩ ስውር ስፍራዎች ብዙ ወጣቶች በደኅንነቶች ታፍነው በጅምላ ታስረው ሰቆቃ እየተፈጸመባቸው  መሆኑንም ምንጮቻችን ተናግረዋል።

በሌላ በኩል የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በ6 ወራት ይነሳል ተብሎ ቀደም ብሎ በገዢው ፓርቲ የተሰጠው መግለጫ ሊራዘም እንደሚችል አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ተናግረዋል። አቶ ሃይለማርያም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከመነሰቱ በፊት የአገሪቱን ዘላቂ ሰላም ማረጋገጥ እና ህዝቡ አዋጁ ላይ ያለውን ሃሳብ ማድመጥ ተገቢ ነው ብለዋል።

አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በኢኮኖሚ፣ ልማት፣ ሰላምና አጠቃላይ ሁኔታ ላይ ምንም አይነት ጉዳት አላደረሰም ሲሉ አቶ ሃይለማርያም ተናግረዋል። ይሁን እንጅ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በኢትዮጵያ ውስጥ ህዝባዊ አመጽ ከተነሳበት ጊዜ ጀምሮ የውጭ ኢንቨስትመነትና የቱሪዝም ገቢ ተዳክሟል። ከዚሁ ጋር ተያይዞም የዶላር ዋጋ አሻቅቧል። በአገሪቱ ውስጥ የዋጋ ንረትም በከፍተኛ ሁኔታ እየታየ ነው።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተባለበት ጊዜ ወይም ከዚያ ወዲህ እንዲቀር አለመደረጉ በአገሪቱ ውስጥ ያለው አለመረጋጋት እንደቀጠለ መሆኑን የሚያሳይ ነው ። በአማራ ክልል ለተነሳው ህዝባዊ ተቃውሞ መነሻ በሆነው የጎንደር ከተማ መረጋጋት እንደሰፈነ ለማሳየት ገዢው ፓርቲ የጥምቀት በአልም በደመቀ ሁኔታ ለማክበር ቅስቀሳ ጀምሯል። ብአዴን ራሱ ባሰማራቸው ካድሬዎች አማካኝነት ለበአሉ ልዩ ዝግጅት እንዲደረግ እየቀሰቀሰ ሲሆን፣ በህዝቡ በኩል ያለው ስሜት ግን አገዛዙ ከሚፈልገው በተቃራኒ ነው። የመስቀል በአል እጅግ በቀዘቀዘ ስሜት እንደተከበረው ሁሉ የጥምቅት በአልንም በተመሳሳይ መንገድ ለማክበር ፍላጎት አለ።