በአልጣሽ ፓርክ የነጻነት ሃይሎችን ለማጥቃት የተላኩ ወታደሮች ከፍተኛ ጉዳት ደረሰባቸው

ጥር ፭ (አምስት)ቀን ፳፻ / ኢሳት ዜና :- ምንጮች ለኢሳት እንደገለጹት በሰሜን ጎንደር ዞን በቋራ ወረዳ አልጣሽ ብ/ፓርክ ውስጥ ለነጻነት የሚታገሉ ሃይሎችን ለመውጋት በሚል የተላኩት ወታደሮች የተወሰኑት ሲሞቱ አብዛኞቹ ደግሞ ከፈተኛ  ጉዳት ደርሶባቸዋል።

በ3 ቡድን ተከፍሎ ለጥቃት ወደ ፓርኩ ከገቡት የሰራዊት አባላት መካከል   አብኑን ወይም አምዶክ ተብሎ በሚጠራዉ አካባቢ የገቡት ወታደሮች  የተጓዙት የእግር መንገድ ከመርዘሙና አብኑን ላይ አለ የተባለው ውሃ ባለመገኘቱ ለከፍተኛ የውሃ ጥም ተደርገዋል። ይህ ተከትሎ ወታደሮቹ  ውሃ ፍለጋ ሲባዝኑ እርስ በርስ አለመግባባት መፈጠራቸውን ምንጮች ይናገራሉ።

አለመግባባቱ ሰፍቶ ሶስት ወታደሮች እርስ በርስ ተታኩሰው ሲገዳደሉ፣ ከ75 በላይ የሚሆኑት ደግሞ ተስፋ ቆርጠው ተበታትነዋል። አሳሽ ሃይሉ መጥፋቱ ከተነገረ በሁዋላ በተደረገው የሄሊኮፕተር አሰሳ  57 ወታደሮች ክፉኛ ተጎድተውና ተጎሳቁለው ተገኝተዋል። እነዚሁ ወታደሮች በአሁኑ ሰአትም በባህርዳር ህክምና እየተደረገላቸው ይገኛል። የ7ቱ የመከላከያ አስከሬን ደግሞ በፍለጋ የተገኘ ሲሆን  የ11 ወታደሮች የደህንነት ሁኔታ ግን እስካሁን አልታወቀም። ከ7ቱ ሟች ወታደሮች መካከል የ6 ቱ አስከሬን የተገኘው ሱዳን ውስጥ  ዲንዲር እየተባለ በሚጠራው ብሄራዊ ፓርክ ውስጥ ነው።

ኢሳት በጅጅጋ በተደረገው የከፍተኛ ወታደራዊ አዛዦች ስብሰባ ላይ አንድ ሻምበል ጦር መጥፋቱን በተመለከተ ሪፖርት ተደርጎ እንደነበር በሳምንቱ መግቢያ ላይ መዘገቡ ይታወቃል።