“ በተለይ ጊዜው ለትግራይ አስተማማኝ አይደለም” ሲል ብአዴን አስታወቀ

የካቲት ፩ ( አንድ )ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ብአዴን ሰሞኑን በክልሉ የተደረጉ ስብሰባዎችን በማስመለክት ባወጣው የማጠቃለያ ሪፖርት ላይ “ የሰላም መናጋት ለገዢው ፓርቲ አመራሮች ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ህብረተሰብ የሚተርፍ ነው። በተለይ ለትግራይ ጊዜው አስተማማኝ አይደለም” ሲል ገልጿል።
“የትግራይ ህዝብ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ማበር ካልቻለ በስተቀር፣ ጊዜው አስተማማኝ” አይደለም የሚለው ብአዴን፣ የክልሉ ህዝብ በህወሃት ላይ ያለውን ጥላቻ በሪፖርቱ ላይ አካቷል።
“በህዝቦች መካከል መጠራጠርን እንዲፈጠር የሚያደርጉ የጥፋት ሀይሎችን በጋራ መታገል የሁሉም ዜጋ ግዴታ ነው” የሚለው ብአዴን፣ የሰላም መናጋት ለገዥው ፓርቲ አመራሮች ብቻ ስጋት አይደለም፣ የሁሉንም ህብረተሰብ የእለት ተእለት ኑሮ የሚያዛባ በፈለግነው ቦታ ተዘዋውረን ሰርተን መመለስ የማንችልበት እድል ይፈጠራል” ብሎአል።
ሪፖርቱ አብዛኛው የብአዴን መካከለኛና ዝቀተኛ አመራርና አባላት በህወሃት ላይ ያላቸውን ቅሬታና ጥላቻ የሚያመልክት ነው። ከጥቂት አመራሮች በስተቀር አብዛኞቹ የብአዴን አባላት ከህወሃት ጋር ያላቸው ልዩነት እየሰፋ በመምጣቱ በሁለቱ ድርጅቶች መካከል ተናቦ መስራት እየቀረ ነው።
በተለይ ከደህንነት ጋር በተያያዘ በመካከለኛና ዝቅተኛ ደረጃ የሚገኙ የብአዴን የደህንነት አባላት ከህወሃት የደህንነት አባላት የሚሰጣቸውን ትእዛዝ ለመቀበል ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ፣ ብዙዎቹን የአማራ ክልል የደህንነት ስራዎች ህወሃቶች ተረክበው እየሰሩ ነው። ምንጮች እንደሚሉት በአሁኑ ሰአት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሰበብ ህወሃት የክልሉን የደህንነት ክፍል ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥሮታል።
ስርዓቱን ለማገልገል እና ለመታዘዝ ፈቃደኛ አይደሉም የተባሉ ከባህርዳር 11፣ ከጎንደር 13፣ ከደብረማርቆስ 9 የደህንነት አባላት ከስራቸው የታገዱ ሲሆን፣ በቦታቸው 39 የህወሃት አባላት ሃላፊነቱን ወስደው የክትትል ስራ እየሰሩ ነው።
የአማራ ተወላጅ የደህንነት አባላት ለመታገዳቸው ምክንያት ሆኖ የቀረበባቸው “በክልሉ ስላለው የጸጥታ ሁኔታ በየጊዜው ሪፖርት አያቀርቡም፣ በክልሉ የሚፈጸሙ ጥቃቶችን እያወቁ እንዳላወቁ ሆነው ያልፋሉ እንዲሁም የሚሰጣቸውን የክትትል ስራ በአግባቡ መስራት አይችሉም” የሚል ነው።
ከፌደራል የተላኩ የኮማንድ ፖስት አባላት ሰሞኑን ባደረጉት ግምገማ በክልሉ ያለው የጸጥታ ሁኔታ አስተማማኝ ባለመሆኑ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አይነሳ የሚል ሃሳብ ማቅረባቸውን ኢሳት መዘገቡ ይታወቃል።